በሳውዲ አረቢያ መንግሥት ባለፈው አንድ ሳምንት ውስጥ ብቻ በተከናወነ መጠነኛ የአፈሳ ዘመቻ ከ14,600 በላይ ሕገ-ወጥ ነዋሪዎች ከአገር መባረራቸውን የሳውዲ አረቢያ መንግስት አስታወቀ። በዚህ የቁጥጥር ዘመቻ በድንበር ጥሰት ከተያዙት መካከል አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን መሆናቸው ተገልጿል።
የሳውዲ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደገለፀው ፣ ከታህሳስ 30 እስከ ጥር 6 2018 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ የመኖሪያ፣ የሥራ እና የድንበር ደኅንነት ሕጎችን በመጣስ በአጠቃላይ 18,054 ሰዎች በቁጥጥር ሥር ውለዋል።
ከእነዚህም መካከል በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ወደ ሳውዲ አረቢያ ለመግባት ሲሞክሩ የተያዙት 1,491 ሰዎች ሲሆኑ፣ ከእነዚህ ውስጥ 59 በመቶው (ወደ 880 የሚጠጉ) ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ካፒታል ጋዜጣ ያገኘዉ መረጃ አመልክቷል።
የተቀሩት 40 በመቶ የመንውያን ሲሆኑ፣ 1 በመቶው ደግሞ የሌሎች አገራት ዜጎች ናቸው።
በተጠቀሰው አንድ ሳምንት ውስጥ ብቻ 14 ሺህ 621 ሕገ-ወጥ ነዋሪዎች ከአገር እንዲወጡ የተደረገ ሲሆን፣ ሌሎች 19 ሺህ 835 ተላላፊዎች የጉዞ ሰነድ እንዲያገኙ ወደየአገራቸው ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ተመርተዋል።
የሳውዲ አረቢያ መንግሥት ለማንኛውም ሕገ-ወጥ ስደተኛ መጠለያ፣ መጓጓዣ ወይም የሥራ ዕድል የሚሰጡ ግለሰቦች እስከ 15 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እና እስከ 1 ሚሊዮን ሪያል በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ እንደሚቀጡ በድጋሚ አስጠንቅቋል።
በአሁኑ ወቅት 27 ሺህ 518 የውጭ አገር ዜጎች (25 ሺህ 552 ወንዶች እና 1 ሺህ 966 ሴቶች) ሕጋዊ ርምጃ ተወስዶባቸው የመባረር ሂደታቸውን በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል።
