የአማራ ክልልን እና የፌዴራል መንግሥታትን በኃይል ለማስወገድ ተንቀሳቅሰዋል በሚል የሽብር ወንጀል ክስ ከተመሰረተባቸው ግለሰቦች መካከል ሶስቱ በዋስትና መለቀቃቸውን የተከሳሾቹ ጠበቃ የሆኑት አቶ ሰለሞን ገዛኸኝ ተናገሩ።
እያንዳንዳቸው 200 ሺህ ብር ዋስትና በማስያዝ ከተለቀቁት ተከሳሾች ውስጥ የኢዴፓ ከፍተኛ አመራር እና የፓርላማ አባል የነበሩት አቶ አብዱራህማን አህመዲን እንደሚገኙበት ጠበቃው ገልጸዋል።
የፌደራል ዐቃቤ ሕግ አቶ አብዱራህማንን ጨምሮ በ23 ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ የመሰረተው በሰኔ 2016 ዓ.ም ነበር።
ለእስር ከተዳረጉ ሁለት ዓመት ሊሞላቸው ከሶስት ወራት ያነሰ ጊዜ የሚቀራቸው ተከሳሾቹ፤ በቀረበባቸውን የሽብር ክስ ላይ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሲከራከሩ ቆይተዋል።
ክሱን ሲመለከት የቆየው የጸረ ሽብር እና ህገ መንግስታዊ ጉዳዮች ችሎት፤ ዐቃቤ ህግ ክሱን እንዲያሻሽል ባለፈው ጥቅምት ወር መጨረሻ ትዕዛዝ መስጠቱን የተከሳሾቹ ጠበቃ አቶ ሰለሞን ገልጸዋል።
ክሱ ተሻሽሎ ከቀረበ በኋላ፤ በከሳሽ እና በተከሳሾች መካከል ባለፈው ህዳር ወር አጋማሽ የዋስትና ክርክር መደረጉን ጠበቃው አስረድተዋል።
የግራ ቀኙን ክርክር ያዳመጠው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ችሎት፤ ዐቃቤ ሕግ ባሻሻለው ክስ ላይ የጠቀሰው የጸረ – ሽብር ድንጋጌ የዋስትና መብት የማያስከለክል በመሆኑ ክሳቸውን በውጭ ሆነው እንዲከታተሉ ለሶስቱ ደንበኞቻቸው ዋስትና መፍቀዱንም አክለዋል።
ተከሳሾቹ በፍርድ ቤት እንዲያሲዙ የተላለፈባቸውን የ200 ሺህ ብር ዋስትና በመክፈል፤ በዚያኑ ዕለት ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት መለቀቃቸውን አቶ ሰለሞን ተናግረዋል።
ሆኖም ተከሳሾቹ በማረሚያ ቤቱ በር ላይ ሲጠብቋቸው ነበር በተባሉ “የፌደራል ፖሊስ አባላት” ተይዘው፤ ለቀናት ያሉበት ሳይታወቅ ቆይተው እንደነበር ጠበቃው አስታውሰዋል።
ኢትዮጵያ ኢንሳይደር
