የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳለማው በሰጡት መግለጫ ከህዳር 2013 ጀምሮ ቤት ለመስራት የሚሆኑ ማህበራት እንዳይደራጁ በካቢኔ ተከልክሎ እንደነበር አስታውሰዋል።
በአሁኑ ጊዜ እገዳው እንደተነሳ የገለጹት ተ/ም/ከንቲባው ለ500 ማህበራት ለቤት መስሪያ የሚሆን ቦታ ለመስጠት ከተማ አስተዳደሩ መዘጋጀቱን ገልፀዋል።
አቶ ጎሹ አክለውም ማህበራቱ በ3 ምዕራፍ እንደሚደራጁ የተገለፀ ሲሆን
- በመጀመሪያ ዙር የመንግስት ሰራተኞች፣
- በሁለተኛ ዙር የፀጥታ ሃይሎች ሲደራጁ
- በመጨረሻው ዙር ነዋሪዎች እንደሚደራጁ ተናግረዋል።
ነዋሪዎች በመጨረሻ ላይ እንዲሆኑ የተደረገው ከመታወቂያ ጋር በተያያዘ መሆኑንም ከንቲባው ገልፀዋል።
ከንቲባው የነዋሪነት መታወቂያው ችግር አለበት ያሉ ሲሆን ብዙ ሃሰተኛ መታወቂያዎችን የያዙ ግለሰቦች መኖራቸውን ገልፀዋል። በተጨማሪ መታወቂያውን የከተማዋ ነዋሪ ያልሆኑ ሰዎች እንደሚጠቀሙቀበትም ነው ያነሱት።
ችግሩን ለመቅረፍም ከክልሉ የቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በመሆን ሶፍትዌር በማልማት አሁን ያለውን መታወቂያ ሙሉ ለሙሉ በመቀየር በዲጂታል ለመተካት ዝግጅት መጠናቀቁን ተ/ም/ከንቲባው ተናግረዋል።
ማህበራት ሲደራጁም ህጋዊ በሆነ መልኩ የከተማ አስተዳደሩ በሰየማቸው ኮሚቴዎች እና ቢሮ በኩል መሆን እንዳለበት ያሳሳቡ ሲሆን ህብረተሰቡ ከሀሰተኛ ደላሎች ራሱን እንዲጠብቅ አሳስበዋል።
ከንቲባው በ2013 የቤት ማህበራት እንዳይደራጁ ከተከለከሉ በኋላ 936 ህገወጥ ማህበራት መደራጀታቸውን የገለፁ ሲሆን እነዚህ ማህበራት እውቅና የላቸውም ብለዋል። ማኅበራቱ በአሁኑ ግን ህጋዊ መንገዱን ጠብቀው ዳግም መደራጀት ይችላሉ ብለዋል።
መረጃው የከተማው ኮሚኒኬሽን ቢሮ ነው።
