በሀገሪቱ የፋይናንስ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ አውቶሜትድ ሥርዓት የሚካሄደው ግብይቱ በኢትዮጵያ የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ መድረክ ላይ ሁሉም ንግድ ባንኮች ስለ ገበያው እኩል መረጃ ኖሯቸው የሚከናወን መሆኑን ብሔራዊ ባንክ በይፋዊ መግለጫው አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ዶ/ር ኢዮብ ተካልኝ፣ “ለተሳታፊ ሁሉ ግልጽ፣ ፈጣንና በመመሪያ የተመራ የገበያ አካባቢ ይፈጥራል። መድረኩ የገበያ ዲሲፕሊንን ለማጠንከር፣ የዋጋ ሂደትን ለማሻሻልና የፋይናንስ ገበያ ሪፎርምን ለመደገፍ ትልቅ ግብዓት ነው።” ሲሉ በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ ተናግረዋል፡፡
የገበያው አሠራር በብሔራዊ ባንክ መመሪያዎች የሚመራ ሲሆን፣ ሁሉም ተሳታፊ ባንኮች የተቀመጡ የሥነ-ምግባር ደንቦችን እና የውጭ ምንዛሬ ተጋላጭነት ገደቦችን የማክበር ግዴታ እንዳለባቸው ተጠቁሟል።
ይህ እርምጃ የኢትዮጵያን የፋይናንስ ገበያ ከዓለም አቀፍ አሠራሮች ጋር ለማጣጣም እና የውጭ ምንዛሬ አስተዳደርን ይበልጥ ዘመናዊ ለማድረግ ያለመ መሆኑም ተመላክቷል።
