የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ስምረት (ስምረት) ባወጣው ወቅታዊ መግለጫ፣ በክልሉ ውስጥ የሚንቀሳቀስ አንድ “የጥፋት ቡድን” ሲል የጠራው አካል የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት በመጣስ ዳግም ጦርነት እየለኮሰ ነው ሲል ከሰሰ።
ድርጅቱ በመግለጫው እንዳመለከተው፣ ይህ ቡድን የህዝቡን ግዛታዊ አንድነትና የተፈናቃዮችን ጥያቄ እንደ ሽፋን በመጠቀም የራሱን ጠባብ ፖለቲካዊ አጀንዳ ለማስፈጸም እየተንቀሳቀሰ ይገኛል።
ቡድኑ ከውጭ ኃይሎች ጋር በመመሳጠር በትግራይ አጎራባች በሆኑት ዓፋርና አማራ ክልሎች አቅጣጫ ወታደራዊ ትንኮሳዎችን መጀመሩንም ስምረት በዝርዝር አስፍሯል።
በመግለጫው ቡድኑ የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ሙሉ በሙሉ በማፍረስ፣ ከኤርትራው የህግደፍ ስርዓት ጋር በሚስጥር በማበር ቀጠናውን ወደ አዲስ ግጭት እየመራው መሆኑ ተገልጿል።
“በወጣቶች ህይወት መቆመር ይብቃ” ያለው ስምረት፣ ቡድኑ የድሃ ልጆችን ለጥይት ሲሳይ በማድረግ ከተጠያቂነት ለማምለጥ እየሞከረ ነው ሲል ወንጅሏል።
በተለይም በፀለምቲ አቅጣጫ የተጀመረው ውጊያ የውጭ ኃይሎችን እቅድ ለማሳካትና የፌዴራል መንግስቱን በኃይል ለመገልበጥ ያለመ መሆኑን ድርጅቱ ገልጿል።
ቡድኑ የጦርነት ዝግጅቱን ለማጠናከር የመንግስትና የህዝብ የሆኑ የተፈጥሮ ሀብቶችንና መሬቶችን ለባለሀብቶች ያለአግባብ እየቸረ መሆኑን ጠቁሞ፣ በዚህ ተግባር ላይ የተሰማሩ አካላት በህግ እንደሚጠየቁ አስጠንቅቋል።
ስምረት በመግለጫው የትግራይ ሰራዊት አባላት በማይመለከታቸውና ለሌሎች አጀንዳ በሚካሄድ ጦርነት ውስጥ እንዳይማገዱና ነፍሳቸውን እንዲያድኑ ጥሪ አቅርቧል።
የትግራይ ህዝብም ልጆቹን ከዚህ የጥፋት ሰልፍ እንዲያስወጣ አሳስቧል።
በመጨረሻም ድርጅቱ፣ የግዛታዊ አንድነትና የተፈናቃዮች ጉዳይ በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ ብቻ መፈታት እንዳለበት በመግለጽ፣ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በሰላም አደናቃፊዎች ላይ አስፈላጊውን ጫና እንዲያደርግ ጠይቋል።
