የጋምቤላ ከተማን ጨምሮ የፀጥታ ችግር በሚስተዋልባቸው የክልሉ አካባቢዎች፣ ከዛሬ ታህሳስ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የሚተገበር የሰዓት እላፊ ገደብ መጣሉን የክልሉ መንግስት አስታወቀ።
የክልሉ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ መሠረት፣ ሰሞኑን በክልሉ በተከሰተው የፀጥታ መደፍረስ ምክንያት ለህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል ከምሽቱ 2:00 ሰዓት ጀምሮ እስከ ንጋቱ 12:00 ሰዓት ድረስ ማንኛውም እንቅስቃሴ የተገደበ ይሆናል።
በዚህ የሰዓት ገደብ ውስጥ ከተፈቀደላቸው የጸጥታ አካላት ውጪ ማንኛውም ሰውም ሆነ ተሽከርካሪ መንቀሳቀስ በጥብቅ የተከለከለ መሆኑ ተገልጿል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ ከተመደቡ የፀጥታ ኃይሎች ውጪ በማንኛውም ቦታ ጦር መሳሪያ ይዞ መንቀሳቀስ የማይቻል መሆኑን ያስታወቀው የክልሉ መንግስት፣ ገደቡ ላልተወሰነ ጊዜ እንደሚቆይም አመላክቷል።
በክልሉ አስተማማኝ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን የህብረተሰቡ ክፍል የተጣሉ ክልከላዎችን በማክበር እና በማስከበር በኃላፊነት መንቀሳቀስ እንዳለበት ጥሪ ቀርቧል።
