በጎንደር ከተማ በ2018 ዓ.ም በሚከበረው የጥምቀት በዓል ከ2 ሚሊዮን በላይ ጎብኝዎች እንደሚጠበቁ የከተማዋ የቅርስ ጥበቃ ተቋም ለመናኸሪያ ሬዲዮ አስታውቋል።
ከጥር 2 እስከ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም በከተማዋ የተለያዩ አውደ ርዕዮች መዘጋጀታቸውን የገለጹት የጎንደር ዓለም አቀፍ የቅርስ አስተዳደር መሪ አቶ ጌታሁን ስዩም፤ በዓሉን ለማክበር ከ2 ሚሊዮን በላይ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ጎብኝዎች እንደሚጠበቁ ተናግረዋል።
ክብረ በዓሉ “ኢትዮጵያን በጎንደር” በሚል መሪ ቃል እንደሚከበር የጠቀሱት አቶ ጌታሁን፤ ለሀገራቸው መስዋዕትነት የከፈሉ ኢትዮጵያውያን የሚመሰገኑበት ልዩ መድረክ መዘጋጀቱንም ገልጸዋል።
በከተማዋ ወደ 15 የሚጠጉ ባለኮከብ ሆቴሎች መኖራቸውን ያነሱት መሪው፤ ከ200 በላይ በኮከብ ደረጃ ያልተቀመጡ ሆቴሎችም እንግዶችን ለመቀበል ዝግጅት ማድረጋቸውን ተናግረዋል። ሆቴሎቹ እንግዶችን በመደበኛ ዋጋ እንዲያስተናግዱ ውሳኔ መተላለፉንም አክለዋል።
በከተማዋ ምንም ዓይነት የፀጥታ ስጋት አለመኖሩን የገለጹት አቶ ጌታሁን፤ ለጎብኝዎች ደህንነት የከተማዋ ፖሊስ ሙሉ ኃላፊነት መውሰዱን ጠቁመዋል። በዓሉን ምክንያት በማድረግ ወደ ከተማዋ ይገባሉ ተብለው የሚጠበቁ እንግዶች ቁጥር ከሆቴሎች የመኝታ አቅም ጋር የማይመጣጠን በመሆኑ “አንድ እንግዳ ለአንድ ቤተሰብ” የሚል አሰራር መዘርጋቱንም አስታውቀዋል።
የእንግዶችን የቆይታ ጊዜ ለማራዘም የተለያዩ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውንና ለዚህም የዘርፉ ባለሙያዎች በሥራ ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል።
በተያያዘ መረጃ በአማራ ክልል ከታህሳስ 28 እስከ ጥር 30 ቀን 2018 ዓ.ም በሚከበሩ ክብረ በዓላት ላይ ከ3 ሚሊዮን በላይ ጎብኝዎች እንደሚጠበቁ የክልሉ ባሕል፣ ቱሪዝም እና ስፖርት ቢሮ ለመናኸሪያ ሬዲዮ ማስታወቁ ይታወሳል።
