በ31ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሀ ግብር በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት ሲደረጉ ማንችስተር ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ የሚያደርጉት የማንቹርያን ደርቢ ተጠባቂ ሆኗል፡፡
31ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎች ከነገ ጀምረው ሲካሄዱ ነገ 8፡30 ላይ በጉዲሰን ፓርክ ኤቨርተን ከአርሰናል በሚያደርጉት ግጥሚያ ጅማሮውን ያደረጋል፡፡
ብራዚላዊውን ተከላካይ ጋብርኤል ማጋሀሌስን እስከ ውድድር አመቱ መጨረሻ በጉዳት ያጡት መድፈኞቹ በቶፊሶቹ ሊፈተኑ እንደሚችሉ ሲጠበቅ በሳምንቱ አጋማሽ በፉልሀም ላይ ያስመዘገቡትን ድል ለመድገም ይፋለማሉ፡፡
እሁድ የሊጉ መሪ ሊቨርፑል ፉልሀምን ከሜዳው ውጭ ወደ ክራቨን ኮቴጅ አቅንቶ 10፡00 ላይ ሲገጥም ብራዚላዊው ወሳኙ ግብ ጠባቂ አሊሰን ቤከር ወደ ቋሚ 11 እንደሚመለስ ይጠበቃል፡፡
ቀያዮቹ ከፊታቸው የሚጠብቋቸውን 4 ጨዋታዎች ማሸነፍ ከቻሉ ሻምፒዮን መሆናቸውን ያረጋግጣሉ፡፡
በተመሳሳይ ሰአት በሳምንቱ አጋማሽ ቶተንሃምን በመርታት 4ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ቼልሲ ወደ ጂቴክ ኮምዩኒቲ ስታድየም አቅንቶ ለታላላቅ ክለቦች ፈታኝ የሆነው ብሬንትፎርድን ይገጥማል፡፡
ምሽት 12፡30 ላይ የሳምንቱ ታላቅ ጨዋታ ኦልድትራፎርድ ላይ ሲደረግ በማንቹርያን ደርቢ ማንችስተር ዩናይትድ የከተማ ተቀናቃኙ ማንችስተር ሲቲን ያስተናግዳል፡፡
በቁርጭምጭሚት ጉዳት ለ7 ሳምንታት ያህል ከሜዳ የራቀው ኖርዌያዊው የማንችስተር ሲቲ አጥቂ አርሊንግ ሀላንድ ከጨዋታው ውጭ መሆኑን አስቀድሞ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ማንችስተር ዩናይትድ ለጨወታው የትኬት ዋጋ ቅናሽ ማድረጋቸውን ተዘግቧል፡፡
ሀገሬ ቲቪ
