አዳማ ፖስታ ቤት የሚገኘው ቲታስ ሕንጻን ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል ለሆስፒታል አገልግሎት ንብ ባንክ ባወጣው ጫረታ መሰረት ተወዳድሮ አሸንፎ ገዝቶታል። አዳማ ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል በር ላይ የሚገኘው ባለ 8 ወለል ቲታስ ሕንጻ በካቴድራሉ በር ላይ የሚገኝ ሲሆን ለሆስፒታል አገልግሎት እንደታሰበ የካቴድራሉ አስተዳዳሪ መልአከ ምህረት ቆሞስ አባ ዜናማርቆስ ተናግረዋል።
ካቴድራሉ እንደ ሀገረ ስብከት ትልቅ ካቴድራል እና ብዙ ምእመናን የሚገለገሉበት ሲሆን ነገር ግን ራስ አገዝ ገቢ ማስገኛ አልነበረውም። አሁን ይህን አጋጣሚ በመጠቀም ንብ ባንክ ባወጣው ጫረታ በመሳተፍ ካቴድራሉ አሸናፊ ሆኗል። ይህ ሲሆን ግን ሙሉ ክፍያ ለመክፈል የሚያስችል ብር አልነበረውም። ቅዱስ ገብርኤል ብዙ ልጆች እንዳሉት እና ይሄን መክፈል እንደሚቻል በማመን እንጂ።
በዚህም መሰረት ጥር 2 እስከ ጥር 5/2018 ዓ/ም ለተከታታይ 4 ቀናት በካቴድራሉ ግቢ ታላቅ መንፈሳዊ ባዛር ተዘጋጅቷል። መንፈሳዊ ባዛሩን የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ባርከው አስጀምረውታል። የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ኃላፊዎች ፣የገዳማት እና የአድባራት አስተዳዳሪዎችም የዚህ ባዛር ተሳታፊ ሆነዋል።
ይህ መንፈሳዊ ባዛር ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት የሚቀጥል ስለሆነ በአዳማ እና በዙሪያው የምትገኙ የቅዱስ ገብርኤል ወዳጆች ለነፍሳችሁ ፈውስ ስታገኙበት የነበረው ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል ነገ ደግሞ ስጋችሁን የምትፈወሱበትን ሆስፒታል እውን ለማድረግ እየተሰራ ስለሆነ የዚህ ስራ ተሳታፊ እንድትሆኑና በባዛሩ ላይ እንድትገኙ ጥሪ ተላልፏል።
Menker Media
