“በድርጅቱ ውስጥ በታዛቢነት የመሳተፍም ሆነ
መልሶ አባል የመሆን ዕቅድ የለንም “
አሜሪካ ከዓመት በፊት በሰጠችው ቅድመ ማስጠንቀቂያ መሠረት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አካል ከሆነው የዓለም የጤና ድርጅት (WHO) አባልነት በይፋ ለቅቃ ወጣች።
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሁለተኛ ዙር የሥልጣን ዘመናቸውን በጀመሩበት ዕለት ካስተላላፏቸው ፕሬዚዳንታዊ ውሳኔዎች መካከል አንዱ የሆነው ከዓለም ጤና ድርጅት መውጣት ተግባራዊ ሆኗል።
ይህንን ውሳኔ ተከትሎ የአሜሪካ ሰንደቅ ዓላማ ስዊዘርላንድ ጄኔቫ ከሚገኘው የዓለም የጤና ድርጅት ዋና መሥሪያ ቤት እንዲነሳ ተደርጓል። ከዚህ በኋላ አገሪቱ ከዓለም ጤና ድርጅት ጋር የሚኖራት ግንኙነት ውስንና ከተቋሙ መውጣቷን ለማጠናቀቅ በሚያስፈልጉ ጉዳዮች ላይ እንደሚሆን ተነግሯል።
አንድ ከፍተኛ የአሜሪካ መንግሥት የጤና ባለሥልጣን፤ “በድርጅቱ ውስጥ በታዛቢነት የመሳተፍም ሆነ መልሶ አባል የመሆን ዕቅድ የለንም ” ሲሉ ተናግረዋል።
ይህ የአሜሪካ እርምጃ የዓለም ጤና ድርጅትን በባጀት ረገድ ክፉኛ እንደሚፈትነው ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ መላ እንቅስቃሴውንም እንደሚያሽመደምደው ይታመናል፡፡ ለመሆኑ ድርጅቱ ለዚህ አደጋ ምን መላ አበጅቶ ይሆን? የዚህ ሰለባ የሚሆኑት ከሁሉም በላይ ድሆቹ የአፍሪካ አገራት በመሆኑ ጉዳዩ በቀጥታ ይመለከተናል፡፡
