አብን በሀገራዊ ምክክሩ ማጠቃለያ ላይ የተፈጸመውን “ሕገ-ወጥ ጣልቃ-ገብነት” በመቃወም ኮሚሽኑ ማብራሪያ እንዲሰጥ ጠየቀ
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በሀገራዊ የምክክር ሂደቱ ማጠቃለያ ላይ የተፈጸሙ ጥሰቶችን፣ አድሏዊ ጣልቃ-ገብነቶችን እና በጀርባ በር የተጨመሩ አጀንዳዎችን አጥብቆ እንደሚቃወም ገለጸ።
አብን ባወጣው መግለጫ፣ ሂደቱን በገለልተኝነት እንዲመሩ አደራ የተጣለባቸው አካላት፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ጥቂት የኮሚሽኑ አባላትና አስተባባሪዎች በግልጽ ወገንተኝነትና ሴራ ሂደቱን ለማስተጓጎል መስራታቸውን ገልጿል።
በስምንቱም አጀንዳዎች ላይ በምክክር የተደረሰባቸው የውሳኔ ሀሳቦች በይፋ ከተነበቡ በኋላ፣ አንድ ኮሚሽነር በጉባኤው ያልተመረመረና በጀርባ በር የተዘጋጀ አጀንዳ ይዘው በመውጣታቸው ምክንያት በርካታ ተሳታፊዎች መድረኩን ረግጠው መውጣታቸውን ፓርቲው ይፋ አድርጓል።
ንቅናቄው ለምክክር ሂደቱ ሙሉ ይሁንታ የሚሰጠው ኮሚሽኑ ስለተፈጸመው ሕገ-ወጥ ጣልቃ-ገብነት፣ ስለተጨመረው አጀንዳ አመጣጥ እና አድሏዊ አቋም ስላራመዱት ኮሚሽነር ድርጊት ለሕዝብ ግልጽና ሕጋዊ ማብራሪያ ሲሰጥ ብቻ መሆኑን አስታውቋል።
አብን በኢትዮጵያ ለሚገኙ የፖለቲካ ችግሮች ሰላማዊ ውይይት ብቸኛ አማራጭ መሆኑን እንደሚያምን ገልጾ፣ እውቅና የሚሰጠውም ጉባኤው ሲወያይባቸው ለቆዩትና አስቀድመው ለሕዝብ ይፋ ለሆኑት ስምንት አጀንዳዎች ብቻ እንደሆነ አረጋግጧል።
መግለጫው የተሰጠው በአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ነሐሴ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ነው
