ከትንሽ ሲሚንቶ ጋር በመቀላቀል ደረጃውን የጠበቀ ቤት ለመገንባት የሚያስችል ጥናት መጠናቀቁን የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ታምራት ሙሉ (ኢ/ር) ለጋዜጣ ፕላስ እንደገለጹት፤ ከሐሮማያ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር የተጠናው ይህ ጥናት ትኩረት ያደረገው በሐረሪ፣ በድሬዳዋ እና በጅግጅጋ አካባቢዎች የሚገኘውን አፈር ለቤት ግንባታ በሚውል መልኩ ማዘጋጀት ላይ ነው።
ቴክኖሎጂው የተለመደውን ብሎኬት ከመጠቀም ይልቅ፣ በአካባቢው የሚገኘውን አፈር ከትንሽ ሲሚንቶ ጋር በመቀላቀል ደረጃውን የጠበቀ ቤት ለመገንባት የሚያስችል ነው ብለዋል።
በእነዚህ አካባቢዎች ለሚኖሩ ከ6 ሚሊዮን በላይ ነዋሪዎች የቤት ግንባታ ችግርን የሚቀርፍ መፍትሔ ይዞ መቅረቡን ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
ግንባታዎች ሙሉ በሙሉ በሲሚንቶ ላይ ብቻ የተንጠለጠሉ እንዳይሆኑ በማድረግ የግንባታ ወጪን በእጅጉ እንደሚቀንስም ተገልጿል።
ጥናቱ ሁሉንም የኢንጂነሪንግ መስፈርቶች አሟልቶ በቤተ-ሙከራ የተረጋገጠ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት “ለአካባቢያዊ ችግር አካባቢያዊ መፍትሔ” በሚል ስትራቴጂ ለመጨረሻ ማረጋገጫ ለውይይት ቀርቧል።
#አዩዘሀበሻ
