የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ ከሱዳን የፋይናንስ ሚኒስትር ጅብሪል ኢብራሂም እና የማስታወቂያ ሚኒስትር ካሊድ አለይሲር ጋር በትላንትናው ዕለት በቀይ ባሕር መረጋጋት እና በቀጠናዊ የደኅንነት ጉዳዮች ላይ መወያየታቸው ተገለጸ።
በኤርትራ ገጠርማ መንደር “ዓዲ ሃሎ” በተካሄደው ውይይት፣ የሁለቱን ሀገራት ጥቅም ለማስከበር እና በአፍሪካ ቀንድ ሰላምን ለማስፈን ቀጣይነት ያለው የፖለቲካ ቅንጅት አስፈላጊነት ላይ ትኩረት ማድረጉን የሱዳን ዜና አገልግሎት ዘግቧል።
በተጨማሪም ውይይቱ የሁለቱን አገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ከማጠናከር ባለፈ፣ በተለያዩ ዘርፎች ትብብርን ማሳደግ በሚቻልባቸው መንገዶች እንዲሁም በቀጠናዊና ዓለም አቀፋዊ ወቅታዊ ክስተቶች ላይ ምክክር መደረጉ ተመልክቷል።
ኢትዮጵያ የባሕር በር ለማግኘት ጥረት ማድረግ መቀጠሏን ተከትሎ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ከቀይ ባህር ዳርቻ ሀገራት ጋር ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር እየሞከሩ ሲሆን በቅርቡም ወደ #ሳውዲ_አረቢያ እና ግብፅ ጉብኝት አድርገዋል።
የኤርትራው መሪ ሀገራቸው ከሱዳን ጋር ያላትን ታሪካዊ ትስስር እና ፀጥታና መረጋጋት ለማምጣት የሚደረገውን ጥረት እንደምትደግፍ ገልጸው፣ የጋራ ተግዳሮቶችን ለመጋፈጥ የትብብር አስፈላጊነት ላይ አፅንዖት ሰጥተዋል።
