በፋሽን ኢንደስትሪው ውስጥ የአፍሪካን ተሰጥኦ ለማጉላት ያለመውና በፈረንሳይ ፓሪስ ከተማ “African Fashion Up 2025” ውድድር ላይ ኢትዮጵያዊቷ ዲዛይነር ሐዊ ሲሳይ ሚደቅሳ አሸናፊ ሆናለች።
ሐዊ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ከተውጣጡ ምርጥ ዲዛይነሮች ጋር በተወዳደረችበት በዚህ ውድድር፣ የፈጠራ ብቃቷን፣ ልዩ የአልባሳት ቅንጅቷን እና ከአፍሪካዊ ማንነት ጋር የተዋሃደውን ዘመናዊ አቀራረቧን በማሳየት የዳኞችን ቀልብ ለመሳብ ችላለች።
የኢትዮጵያዊቷ ሐዊ ሲሳይ ድል የአፍሪካ ፋሽን በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን እውቅና ከፍ የሚያደርግ ነው። ዲዛይኖቿ የአፍሪካን ወግና ታሪክ ከዘመናዊነት ጋር በማጣመር ልዩ የሆነ ውበትን ይፈጥራሉ። ይህ ደግሞ በዓለም አቀፍ የፋሽን ገበያ ላይ የአፍሪካ ዲዛይነሮች ተወዳዳሪነታቸውን ከፍ ያደርጋል – ተብሏል።
የ“African Fashion Up 2025” ውድድር የአፍሪካን ፋሽን ለዓለም ለማስተዋወቅ ያለመ ሲሆን፣ እንደ ሐዊ ሲሳይ ላሉ ብሩህ ተስፋ ላላቸው ዲዛይነሮች ትልቅ መድረክ ሆኖ ያገለግላል።
ሐዊ ያገኘችው ይህ ድል ወደፊት ለሌሎች ወጣትና ታዳጊ ኢትዮጵያውያን ዲዛይነሮች መነሳሳትን የሚሰጥ ከመሆኑም በላይ፣ የኢትዮጵያን ፋሽን ኢንዱስትሪ ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው ይጠበቃል።
እንኳን ደስ አለሽ ኢትዮጵያ
እንኳን ደስ አለሽ ሐዊ
