ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋትን የብሔራዊ ጥቅሟ ወሳኝ አካል አድርጋ እየሰራች ነው ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳም ተስፋዬ ገለጹ።
ኃላፊው ይህን የተናገሩት፤ የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ከተለያዩ የጎረቤት አገራት ለመጡ ዲፕሎማቶች እየሰጠ ባለው ሥልጠና መድረክ ላይ ነው።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳም ተስፋዬ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ “ኢትዮጵያ ብልጽግናን፣ ሰላምንና መረጋጋትን የሚመለከተውን የብሔራዊ ጥቅሟን የቀጣናው እጣ ፈንታ ወሳኝ አካል” አድርጋ ትመለከታለች።
ቀጣናው ሽብርተኝነት፣መፈናቀል፣ የርስ በርስ ግጭትና ሕገወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውር ተግዳሮቶች ያሉበት መሆኑን ጠቅሰው ኢትዮጵያ የቀጣናው ተግዳሮቶች ለመቋቋም በርካታ ጠቃሚ እርምጃዎችን እየተወሰደ መሆኑን መናገራቸውን ኢፕድ ዘግቧል።
የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳም የሥልጠናው አላማ ትብብርን ማጠናከርና በሕዝቦች መካከል ጥልቅ ግንዛቤን ማጎልበት መሆኑን ጠቅሰው፤ በጋራ ችግሮች ላይ የትብብር መድረኮችን መፍጠር እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
ዲፕሎማቶች በዓለም አቀፍ የዲፕሎማሲ መድረክ የጋራ ግቦችን ለማራመድ የሚያደርጉትን የትብብር ጥረቶች መደገፍ አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል።
