አሜሪካ፤ በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት የተሳተፉ ሁሉም ኃይሎች “የጦር ወንጀሎች ፈጽመዋል” የሚል ድምዳሜ ላይ መድረሷን የሀገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን መናገራቸውን ተከትሎ የኢፌዲሪ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫውን በመቃወም መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ አሜሪካ “የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት አባላት፣ የኤርትራ መከላከያ ሰራዊት እና የአማራ ኃይሎች፤ ግድያ፣ አስገድዶ መድፈር እና ሌሎች ጾታዊ ጥቃቶች እና ማሰቃየትን ጨምሮ በሰብዓዊነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን ፈጽመዋል” ብላ መክሰሷን ተከትሎ የኢፌዲሪ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፣ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ጉዳዩን በተመለከተ ያወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን እና የተመድ የሰብአዊ መብት ኮሚሽነር በጋራ ካደረጉት ምርመራ አንፃር ሲታይ ምንም አዲስ ግኝት ያልተካተተበት ነው ብሏል። በመሆኑም የኢትዮጵያ መንግሥት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ያቀረበበትን ባዶ ውግዘት በፍፁም እንደማይቀበለው ገልጿል። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ያወጣው መግለጫ አንድን ወገን ብቻ መወንጀል ላይ ያነጣጠረ መሆኑንም ነው ሚኒስቴሩ በመግለጫ የጠቆመው።
የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ ‹‹ያልተረጋገጡ እና ስም አጥፊ›› ሲል ባወጣው መግለጫ የአሜሪካን የውጪ መሥሪያ ቤት ሪፖርትን ነቅፏል፡፡ ሚኒስቴሩ ‹‹አሜሪካ ከ2009 (እ.አ.አ) ጀምሮ ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳቸውን ለማራመድ በኤርትራ ላይ ሲያደርጉት የነበረውን ያልተገባ ጠላትነት እና ሰይጣናዊ ድርጊት ተቀጥያ ነው›› ሲልም ኮንኖታል። ከአንድ ሳምንት በፊት ወደ አዲስ አበባ መጥተው የነበሩት የአሜሪካው ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒዮ ብሊንከን፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን ጨምሮ ከኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት እና በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በተደረገው የሰላም ስምምነት ህወሓትን በመወከል ፊርማቸው ካኖሩት አቶ ጌታቸው ረዳ ጋር ተገናኘተው መወያየታቸው ይታወሳል።
