በአሁኑ ወቅት በተለይ ኃይለኛ በሆነው የኤል ኒኖ የአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት በአፍሪካ ኢኮኖሚ ላይ ከ10 እስከ 20 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርስ እንደሚችል የአፍሪካ ልማት ባንክ ከፍተኛ የአየር ንብረት ባለሙያ አስጠነቀቁ።
ይህ አስጊ ሁኔታ በአህጉሪቱ ላይ ከፍተኛ የረሃብ አደጋ፣ የምግብ እና የንጹህ ውሃ ዋስትና እጦት እንዲሁም መጠነ ሰፊ ስደት እንዲከሰት ሰፊ እድል እንዳለው ተመላክቷል።
ከዚህም ባለፈ የአየር ንብረት አደጋዎቹ መሠረተ ልማቶችን በማውደም የመንግሥት ግምጃ ቤቶችን እና የባንክ ሥርዓቶችን ለከፍተኛ ፈተና እየዳረጉ ይገኛሉ።
አገራትም የተበደሩትን ብድር ለመክፈል በመቸገራቸውና አደጋውን ለመቋቋም ከጤና፣ ከትምህርት እና ከሌሎች መሠረታዊ የልማት ዘርፎች በጀት በማዘዋወር “የአየር ንብረት የገንዘብ ወጥመድ” ውስጥ እየገቡ መሆናቸው ተገልጿል።
የአፍሪካ ልማት ባንክ አክሎም፣ አህጉሪቱ ከዚህ አውዳሚ የኤል ኒኞ ተፅዕኖ ለመከላከል እና ለመቋቋም በዚህ ዓመት ብቻ እስከ 100 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ከፍተኛ የበጀት ድጋፍ እንደሚያስፈልጋት ገልጿል።
