የእስራኤል ኤምባሲ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እንዲሁም ከኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ጋር በመሆን “የሳይበር ደህንነት ሁኔታ እና እድገት በኢትዮጵያ እና ዓለም አቀፍ ገጽታ” የሚል ርዕስ አውደ ጥናት በዛሬው ዕለት አካሂዷል።
በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብረሃም ንጉሴ ፤ እስራኤል እና ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲ፣ በኢኮኖሚ፣ በጤና፣ በግብርና፣ በትምህርት፣ በባህል እና በሃይማኖት ትስስር ረጅም ጊዜ የዘለቀ የሁለትዮሽ ግንኙነት አላቸው ሲሉ ገልጸዋል።
በዚህም የትብብር ዘርፉን በማስፋት ከኢትዮጵያ ጋር የሳይበር ደህንነት በተመለከተ የመጀመሪያው አውደ ጥናት መሆኑን የገለጹት አምባሳደሩ ሀገራቱ ቀጣይነት ያለው ስራን እንዲሰሩ መሰረት የሚሆን ነው ሲሉ ተናግረዋል።
አንድ ሀገር በዲጅታል ስርዓት በሚጓዝበት ጊዜ የሳይበር ጥቃት በሰፊው የሚደርስ በመሆኑ የሳይበር ደህንነት እውቀት ሊኖር ይገባል ብለዋል።
ኢትዮጵያም ዲጅታል ኢኮኖሚን ለመገንባት በምታደርገው ጉዞ የእውቀት፣ የመረጃ እና ሌሎች የሳይበር ደህንነት ማረጋገጥ የሚቻልባቸውን መንገዶች ለማመላከት ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
የሳይበር ጥቃት በፋይናንስ ተቋማት፣ በመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ በወታደራዊ መዋቅሮች ላይ የሚፈጸም በመሆኑ በምን መልኩ መከላከል ይቻላል የሚለውን እስራኤል ከኢትዮጵያ ጋር ለመስራት ዝግጁ ነች ሲሉ ገልጸዋል።
በአውደጥናቱ የእስራኤል የሳይበር ደህንነት ኩባንያ ምክትል ፕሬዚዳንት አንድሪው ፔሌድ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለግል ዘርፍ ባለሙያዎች እና ሌሎች ባለሙያዎች አውደ ጥናቱን አቅርበዋል።
