ዩናይትድ ኪንግደም “ለፍልስጤም የአገርነት ዕውቅና ለመስጠት ውጥኑ አለኝ” አለች። እስራኤል በጋዛ እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት ካላቆመች ለፍልስጤማውያን የሉዓላዊ ግዛት ዕውቅና ይሰጣቸዋል ብላለች ለንደን።
በመስከረሙ የመንግስታቱ ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ዕውቅናው ሊሰጥ እንደሚችልም ጠቅላይ ሚኒስትር ኬር ስታርመር አሳውቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ካቢኒያቸውን በአስቸኳይ አስጠርተው በጋዛ ጉዳይ ላይ መክረዋል። በሚቀጥሉት ሳምንታት እስራኤል ወሳኝ እርምጃ ትወስዳለች የሚል ተስፋ እንዳላቸውም የካቢኔ ዓባላቱ አስገንዝበዋል።
ፈረንሳይ በኒው ዮርኩ ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ለፍልስጤም ዕውቅና እንደምትሰጥ ይፋ ባደረገች ማግስት ነው እንግሊዝም ይህን ሀሳብ ግልጽ ያደረገችው።
አውሮፓውያን በፍልስጤም ጉዳይ ላይ ተመሳሳይ አረዳድ እንዳላቸውም ያስያል ውሳኔው።
ስታርመር እና ዶናልድ ትራምፕ በተገናኙበት ሰዓት ስለፍልስጤም አገርነት ጉዳይ ሀሳብ አለመነሳቱ ደግሞ የለንደንን ውጥን ጥያቄ ውስጥ ያስገባዋል።
በአሁኑ ሰዓት በጋዛ ያለው የሰብዓዊ ቀውስ መክፋት የምዕራቡን ዓለም ፖለቲከኞች በጉዳዩ ላይ የተከፋፈለ ሀሳብ እንዲኖራቸው አድርጓል።
በጋዛ ከ60 ሺሕ በላይ ሰዎች ህይወታቸውን ሲያጡ በእስራኤል በኩልም ከጋዛው ጋር እኩል ባይታይም ሺዎች አልቀዋል ።
ዘገባው የአልጀዚራ ነው።
