ኢትዮጵያ ከኤርትራ መንግሥት ጋር ያለው ግንኙነት እንዲሻክር ያደረገው ዋናው ምክንያት የቀይ ባሕር ጥያቄ ሳይሆን በትግራይ ጦርነት ወቅት የኤርትራ ጦር የፈጸመው ዘረፋና ውድመት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ በተካሄደው የ6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በንግግራቸውም በሁለቱ አገራት መካከል ችግር የተፈጠረው የኢትዮጵያ መንግሥት የቀይ ባሕር ጥያቄ በማንሳቱ ነው ተብሎ የሚታሰበውና የሚተነተነው ሐሳብ ስሕተት መሆኑን አብራርተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግንኙነቱ እንዲሻክር ያደረጉትን ነጥቦች ሲዘረዝሩ በትግራይ ክልል በነበረው ጦርነት የመጀመሪያ ዙር ውጊያ ወቅት የኤርትራ ጦር “ከጀርባ በመግባት” በፈጸማቸው ተግባራት ጸብ መጀመሩን ገልጸዋል።
እንደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገለጻ የኤርትራ ጦር በአክሱም ወጣቶችን በጅምላ መግደሉ፣ ቤቶችን ማፍረሱ እንዲሁም በዓድዋ ከተማ አካባቢ ፋብሪካዎችን መዝረፉና ማውደሙ ለግንኙነቱ መበላሸት መነሻ ሆነዋል።
ጠቅላይ ሚንስትሩ በማብራሪያቸው ‹‹በወቅቱ ይህንን ድርጊት በወቅቱ ለመቆጣጠር የሚያስችል ሁኔታ እንዳልነበረም›› ሲሉ ለምክር ቤቱ አስረድተዋል።
መንግሥት ከኤርትራ ጋር የነበረውን አለመግባባት ለመፍታትና ሰላም እንዲሰፍን ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ እንደቆየ ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጦርነቱ ወቅት የተፈጸሙት እነዚህ ወንጀሎችና የንብረት ውድመቶች በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ወደ ከፋ ደረጃ እንዳሸጋገሩት ጠቁመዋል፡፡
