ባለፉት ሰባት ወራት ውስጥ ከ343 ቢሊዮን ብር በላይ በድጅታል የገንዘብ ማስተላለፊያ ዘዴ መዘዋወሩ ተገልጿል ።
በገንዘብ ሚኒስቴር የትሬዠሪ እና የመንግስት ሂሳብ መምሪያ ሀላፊ ነጠሩ ወንድወሰን፤ የገንዘብ ሚኒስቴር ወጪ ለመቀነስ፣ ለቅልጥፍና፣ እና ለግልፀኝነት ይረዳ ዘንድ የመንግስት ተቋማት የክፍያ ስርዓትን ማዘመን በሚቻልበት ደረጃ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
መንግስት በብርቱ እየሰራበት ካሉት ተግባራት መካከል አንዱ የዲጂታል ስርዓት ነው ያሉት ሀላፊዋ ይህም በርከት ያሉ ጥቅሞች እንዳሉትም አስረድተዋል፡፡
የዲጅታል የክፍያ ስርዓት ተግባራዊ መሆንን ከጀመረ ወዲህ መንግስት የጥሬ ገንዘብ ለማሳተም የሚያወጣውን ወጪ መቀነስ ተችሏል ብለውናል።
ከዚህ ባለፈ የዜጎችን እንግልትና የጊዜ ብክነት እንዲሁም የደህንነት ስገት ቀርፏል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ለሚፈጸሙ ክፍያዎችን ማዘመን ያስፈልጋል ብላ በህግ ከደነገገች 15 ዓመታት መቆጠራቸውን አንስተዋል።
ሃላፊዋ ይህን ያሉት “ዘመናዊ የአሰራር ስርዓት ለመንግስት የጥሬ ገንዘብ አስተዳደር ጠቀሜታ ” በሚል መሪ ሃሳብ በግምጃ ቤት ነጠላ ሂሳብ ላይ ያተኮረ የምክክር አውደ ጥናት እየተካሄደ ባለበት ወቅት ነው።
