አርሰናል ዛሬ በጆሴ አልቫላዴ ስታዲየም ከስፖርቲንግ ጋር በሚያደርገው የሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍፃሜ የመጀመሪያ ዙር ጨዋታ ላይ ግዮከሬስ የቀድሞ ቡድኑን ይገጥማል።
ይህ ስዊድናዊ ኢንተርናሽናል ባለፈው ክረምት በ63.5 ሚሊዮን ፓውንድ ወደ አርሰናል ከመዛወሩ በፊት፣ ለስፖርቲንግ በ102 ጨዋታዎች 97 ጎሎችን አስቆጥሯል።
የ27 ዓመቱ ግዮከሬስ ወደ ቀድሞ ሜዳው ሲመለስ ደጋፊዎች በጠላትነት ስሜት ሊቀበሉት እንደሚችሉ ቢገመትም የክለቡ ዋና አሰልጣኝ ሩይ ቦርገስ፣ ቪክቶር ግዮከሬስ ወደ ፖርቹጋሉ ክለብ ሲመለስ በደጋፊዎች ተቃውሞ ኢላማ እንደማይሆን ተስፋ አድርገዋል።
አሰልጣኙ እንዲህ ብለዋል፦ “እሱ ታላቅ ተጫዋች ነው፤ በሁሉም ሰው ዘንድም አቀባበል እንደሚደረግለት እርግጠኛ ነኝ፤ ምክንያቱም በስፖርቲንግ ታሪክ ውስጥ አሻራውን ጥሏል፣ ለዚህም እውቅና ሊሰጠው ይገባል።” ብሎዋል
ቪክቶር ግዮከሬስ በኤምሬትስ ጅማሮው ባይቀናውም ስዊድናዊ ተጫዋች አሁን ላይ ምርጥ ብቃቱን ማሳየት ጀምሯል እስካሁን ለአርሰናል 17 ጎሎችንም አስቆጥሯል። በቅርቡ አርሰናል ከኤፍኤ ካፕ በሳውዝሃምፕተን ተሸንፎ በወጣበት ጨዋታ ላይ ተቀይሮ በመግባት ጎል ማስቆጠር ችሏል።
አሐዱ ሬዲዮ
