የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዋሽንግተን ዲሲ እና በኒውዮርክ ባጋጠመው አስከፊ የአየር ሁኔታ ምክንያት ወደ ስፍራዎቹ የሚደረጉ መደበኛ በረራዎችን መሰረዙን ለክቡራን ደንበኞቹ አስታውቋል።
አየር መንገዱ ባወጣው መግለጫ መሠረት በጥር 16 ቀን ከአዲስ አበባ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ የሚደረገው በረራ ቁጥር ET 500 እንዲሁም በጥር 17 ቀን ከዋሽንግተን ዲሲ ወደ አዲስ አበባ የሚመለሰው በረራ ቁጥር ET 501 ተሰርዘዋል።
በተመሳሳይ በጥር 17 ቀን ከአዲስ አበባ ወደ ኒውዮርክ የሚደረገው በረራ ቁጥር ET 514 እና ከኒውዮርክ ወደ አዲስ አበባ የሚመለሰው በረራ ቁጥር ET 515 በአየር ሁኔታው ምክንያት የማይከናወኑ መሆኑ ተገልጿል።
በእነዚህ የበረራ ስረዛዎች ምክንያት ለተቸገሩ መንገደኞች እንደ አስፈላጊነቱ የቦታ ዳግም ምዝገባ፣ የበረራ ጊዜ ሽግሽግ ወይም የክፍያ ተመላሽ አገልግሎቶች እንደሚመቻቹ አየር መንገዱ አረጋግጧል። ተቋሙ ለተጓዦች እና ለበረራ ሰራተኞች ደህንነት ቅድሚያ በመስጠት ሁኔታውን በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን ገልጾ፣ ለተፈጠረው እንግልትም ልባዊ ይቅርታውን አቅርቧል።
ተጓዦች ወደ አየር ማረፊያ ከመጓዛቸው በፊት የበረራቸውን ወቅታዊ ሁኔታ በአየር መንገዱ ድረ-ገጽ ወይም የሞባይል መተግበሪያ በኩል እንዲያረጋግጡ የተመከረ ሲሆን፣ በተጨማሪም በስልክ ቁጥር +251 11 617 9900 ወይም በኢሜይል Reservation@ethiopianairlines.com በማግኘት ዝርዝር መረጃ ማግኘት እንደሚችሉ ተገልጿል።
