የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተጠናቀቀው የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት ከ32.7 ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ ማስመዝገቡንና በአንድ ዓመት ከግማሽ ትሪሊዮን ብር በላይ ተቀማጭ ገንዘብ መሰብሰቡ ተገለጸ፡፡
ባንኩ የ2017 የሒሳብ ዓመት የሥራ አፈጻጸሙን የተመለከተ ሪፖርት እንደሚያሳየው በሒሳብ ዓመቱ ከታክስ በፊት ያስመዘገበው የትርፍ መጠን ከቀዳሚው ዓመት ከ14.2 በመቶ ብልጫ አለው፡፡
የተመዘገበው የትርፍ መጠን በኢንዱስትሪው በከፍተኛነቱ የሚገለጽ ነው፡፡ የባንኩ የቀዳሚ ዓመታት ሪፖርት እንደሚያሳየው በ2016 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት አስመዝግቦት የነበረው ትርፍ 26.7 ቢሊዮን ብር ነበር፡፡
ባንኩ ለመጀመርያ ጊዜ ዓመታዊ ትርፉን ከ20 ቢሊዮን ብር በላይ ማድረስ ችሎ የነበረው በ2014 የሒሳብ ዓመት ሲሆን፣ በወቅቱ ከታክስ በፊት አትርፎ የነበረው 21.8 ቢሊዮን ብር ነበር፡፡ በ2015 ደግሞ ይህንን ትርፍ ወደ 22.1 ቢሊዮን ብር አሳድጎ እንደነበር ይታወሳል፡፡
