በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ውስጥ ተከስቶ የነበረው የማርበርግ ቫይረስ ሙሉ ለሙሉ በቁጥጥር ሥር መዋሉን ተከትሎ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አቋርጦት የነበረውን በረራ እንደሚጀምር አስታወቀ።
በኅዳር ወር መጀመሪያ ላይ በተከሰተው ወረርሽኝ በጂንካ ሆስፒታል ስድስት ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎ ነው በሽታው ማርበርግ መሆኑን መንግሥት ያስታወቀው።
በዚህም ሳቢያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ጂንካ ያደርግ የነበረውን በረራ አቋርጦ የቆየ ሲሆን፣ በአካባቢው በሕዝብ ትራንስፖርት ላይ ሳይቀር ዕገዳ ተጥሎ ነበር።
ከሦስት ወራት በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ዞን የተከሰተው የማርበርግ ቫይረስ አሁን በቁጥጥር ሥር መዋሉን የጤና ሚኒስቴር ጥር 18/2018 ዓ.ም. አስታውቋል።
ይህንንም ተከትሎ አየር መንገዱ ለክልሉ እና ለዞኑ ተቋማት በጻፈው ደብዳቤ ከአዲስ አበባ ጂንካ እና ከጂንካ አዲስ አበባ አቋርጦት የነበረውን በረራ አርብ ጥር 22/2018 ዓ.ም. እንደሚጀምር ከአየር መንገዱ የተጻፈውን ደብዳቤ አያይዞ የዞኑ ኮሚዩኒኬሽን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ አሳውቋል።
የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ እንደተናገሩት ቫይረሱ ከኢትዮጵያ “ጨርሶ እንደተወገደ” ይፋ የተደረገው በዓለም የጤና ድርጅት አሠራር መሠረት ላለፉት “42 ተከታታይ ቀናት ምንም አዲስ ታካሚ ባለመመዝገቡ” ነው።
ማርበርግ ቫይረስ በኢትዮጵያ ውስጥ መከሰቱ ከታወቀ በኋላ በነበሩት ወራት 14 ሰዎች በበሽታው እንደተያዙ በላብራቶሪ ምርመራ ተረጋግጧል። ከመካከላቸውም የዘጠኙ ሕይወት ሲያልፍ አምስት ሰዎች ከበሽታው አገግመዋል።
