የመንግስት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የኢትዮጵያ እዳ እና ሃብት አስተዳደር ኮርፖሬሽንን ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር በመሆን የፊት ለፊት ግምገማ ላማካሄድ ታህሳስ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ለ2:30 ቀጠሮ ይዞ የነበር ቢሆንም፤ የተቋሙን የስራ ኃላፊዎች የመገኘት ግዴታ ቢኖርባቸውም ሳይገኙ ቀርተዋል።
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ መለስ መና የተቋሙ ዋና ስራ አስፈጻሚ የቦርድ ሰብሳቢ እንዲሁም የቦርድ አባላት በተገኙበት የተቋም አደረጃጀት፣ አሰራር ላይ ግልጽነት የሚፈልጉ ጉዳዮች ላይ ፊት ለፊት አስፈላጊ መሆኑ በቋሚ ኮሚቴው በኩል መልእክት እንዲደርስ እና በዚያ ላይ ወይይት ለማካሄድ ቀጠሮ መያዙን አስረድተዋል፡፡
ይሁንና የተቋሙ የስራ ሃላፊዎች እና የቦርድ ተወካዮች በስራ ምክንያት መገኘት እንዳልቻሉ አረጋግጠናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የተቋሙ ኃላፊ እና የቦርዱ ሰብሳቢ በሌሉበት ወይይቱን ማካሄድ ካሰብነው ግብ አንጻር የተሳካ ይሆናል የሚል ግምት ስለሌለን ወይይቱ ወደ ሌላ ቀን ተዘዋውሯል ብለዋል።
የመንግስት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የስራ ኃላፊዎችን አስከ 3:20 ድረስ ጠብቆ ውይይቱን በቀጣይ ሁሉም አካላት በተገኙበት ይካሄዳል ሲል አስረድቷል፡፡
በመድረኩ ላይ የተገኙት ምክትል ስራ አስፈጻሚው በበኩላቸው ተቋሙ ከተቋቋመ አጭር ጊዜ እንደሆነው አስረድተው የተቋሙን ቁመና ለማስተካካል በሌላ ቀን ዋና የስራ ሃላፊዎችም ሆነ ተቆጣጣሪው መስሪያ ቤት በተገኙበት ማካሄድ ይሻላል ካሉ በኋላ ስብሰባው ወደ ሌላ ቀን ተዘዋውሯል፡፡
(ሸገር ራዲዮ)
