የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለ60 ዓመታት ሲያገለግል የቆየውን የፌደራል ወንጀል ሥነ-ሥርዓት ሕግ የሚተካውን፣ አዲሱን የወንጀል ሥነ-ሥርዓት እና የማስረጃ ሕግ አጽድቋል።
ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ መጋቢት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. የጸደቀው አዋጅ ቁጥር 1410/2018 የግለሰቦችን ነፃነት የሚያከብሩ እና የፍትሕ ሥርዓቱን የሚያዘምኑ በርካታ አዳዲስ ድንጋጌዎችን ማካተቱ ተገልጿል።
የሕግ አማካሪ እና ጠበቃ ዳንኤል ፍቃዱ: “አዲሱ ሕግ እንደ የግል ስልክ ጠለፋ እና ድብቅ ክትትል ባሉ የግል ነፃነትን ሊገድቡ በሚችሉ የምርመራ ዘዴዎች ላይ ጥብቅ የፍርድ ቤት ቁጥጥርና የጊዜ ገደብ እንዲቀመጥ አድርጓል።”ሲሉ ተናግረዋል።
በተጨማሪም የባህላዊ ፍርድ ቤቶች ውሳኔዎች የሴቶችን መብት እንደማይጋፉ መደበኛ ፍርድ ቤቶች መርምረው እንዲያጸድቁ የሚያዝ ድንጋጌ ተካቷል ተብሏል።
ሌላኛው የሕግ ባለሙያ አቶ ጀምበር አብዶ በበኩላቸው፣ ተጠርጣሪዎች በምርመራ ወቅት ለሚደርስባቸው አካላዊም ሆነ ስነ-ልቦናዊ ጉዳት ካሳ የሚጠይቁበት ልዩ አሰራር እንደተዘረጋ ጠቁመዋል።
አዲሱ ሕግ የፍርድ ቤቶችን የሥራ ጫና ለመቀነስ የክስ ድርድር ሥርዓትን ያስተዋወቀ ሲሆን፣ ተከሳሾች ጥፋታቸውን አምነው ከዐቃቤ ሕግ ጋር በመደራደር የቅጣት ቅናሽ ማግኘት የሚችሉበትን ዕድል ፈጥሯል ተብሎለታል።
ተከሳሾች ጥፋታቸውን አምነው ከአቃቤ ሕግ ጋር ተነጋግረው ክሱን የሚያቋርጡበት አሰራር ተፈጻሚ የሚሆነው ግን ዳኛው ተከሳሹ ድርድሩን ያደረገው በፈቃደኝነት እና መብቱን ተረድቶ መሆኑን ሲያረጋግጥ ብቻ እንደሚሆን ተገልጿል።
በአጠቃላይ 228 ገጾች እና 444 አንቀጾችን የያዘው ይህ ሕግ፣ ቀደም ሲል ተበታትነው የነበሩ የሥነ-ሥርዓት እና የማስረጃ ሕግጋትን በአንድ ላይ አጠቃሏል።
ሕጉ በከባድ ወንጀሎች ላይ መረጃ የሚሰጡ ምስክሮች የሚጠበቁበትን ማዕቀፍም የዘረጋ ሲሆን፣ የተንቀሳቃሽ ምስል፣ የድምፅ፣ የማኅበራዊ ትስስር ገጾች እና የኮምፒውተር መረጃዎች በክርክር ወቅት እንደ ቀዳሚ ማስረጃ መገልገል እንዲቻል ሕጋዊ ዕውቅና ሰጥቷል።
