የአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ዶክተር አኪንዉሚ አዴሲና አፍሪካ ከድህነት እና ኋላቀርነት ለመውጣት ከፈለገች ጥሬ ዕቃዎችን ወደ ውጭ መላክ ማቆም አለባት ሲሉ አሳስበዋል።
አዴሲና ሐሙስ ዕለት በ ኤክ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት አፍሪካ ያልተዘጋጁ ምርቶችን ከማቅረብ ወደ ተመረቱ እና ተጨማሪ እሴት ያላቸውን እቃዎች አምራችነት መሸጋገር እጅግ አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።
“አፍሪካ ጥሬ ዕቃዎቿን ወደ ውጭ መላክ ማቆም አለባት። ጥሬ ዕቃዎችን ወደ ውጭ መላክ የድህነት በር ነው። ተጨማሪ እሴት ያላቸውን ምርቶች ወደ ውጭ መላክ ደግሞ ወደ ሀብት የሚያደርስ አውራ ጎዳና ነው” ሲሉ ጽፈዋል።
እንደ አሜሪካ የንግድ ተወካይ ቢሮ እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ተቋማት መረጃዎች እንደሚያሳዩት አፍሪካ ከዓለም የማኑፋክቸሪንግ ምርት ውስጥ ከሁለት በመቶ በታች ብቻ ነው የምትይዘው።
ይህ ሁኔታ አፍሪካ በግብርና እና በማዕድን ዘርፎች ከፍተኛ የተፈጥሮ ሀብት ባለቤት ብትሆንም በዓለም ኢኮኖሚ ውስጥ ያላት ሚና አነስተኛ እንዲሆን ምክንያት ሆኗል።
ፕሬዝዳንት አዴሲና አፍሪካ ጥሬ ዕቃዎችን በማቀነባበር የራሷን ኢንዱስትሪዎች በማሳደግ ለዜጎቿ የስራ እድል መፍጠር እና የውጭ ምንዛሬ ገቢዋን ማሳደግ እንደምትችል አስረድተዋል።
