የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በናይጄሪያ፣ በኬንያ፣ በደቡብ አፍሪካ እና በሌሎችም ሀገራት የሚገኙ አምባሳደሮች በአስቸኳይ ከኃላፊነታቸው ተነስተው ወደ ዋሽንግተን እንዲመለሱ ትዕዛዝ አስተላለፉ።
ይህ በድምሩ 30 ሀገራትን ያካተተው የአምባሳደሮች ጥሪ የትራምፕ አስተዳደር የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በአዲስ መልክ ለመቅረጽ የጀመረው ስር ነቀል ለውጥ አካል መሆኑ ተገልጿል።
ከአምባሳደሮቻቸው እንዲነሱ ከተደረጉ የአፍሪካ ሀገራት መካከል በምስራቅ አፍሪካ ቁልፍ ስትራቴጂካዊ አጋር የሆነችው ኬንያ፣ የምዕራብ አፍሪካዋ ግዙፍ ሀገር ናይጄሪያ እና የደቡብ አፍሪካ ቀጠና ተጽዕኖ ፈጣሪዋ ደቡብ አፍሪካ ይገኙበታል።
በተጨማሪም በሰሜን አፍሪካ የሚገኙት ግብፅ እና ሞሮኮ በተመሳሳይ የአምባሳደሮች ጥሪ የተላለፈባቸው ሀገራት ናቸው።
ይህ እርምጃ አዲሱ የአሜሪካ አስተዳደር በየሀገራቱ የራሱን ስትራቴጂ የሚያስፈጽሙ ዲፕሎማቶችን ለመተካት ያለውን ፍላጎት የሚያሳይ ቢሆንም፣ በሀገራቱ እና በአሜሪካ መካከል ያለውን የቆየ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለአጭር ጊዜም ቢሆን ሊያስተጓጉል ይችላል የሚል ስጋት ፈጥሯል።
የአምባሳደሮቹ መነሳት በተለይ በአፍሪካ ቀንድ እና በተቀረው የአህጉሪቱ ክፍል ያለውን የአሜሪካ ተጽዕኖ እና ቀጣይ የትብብር መስኮች ምን ሊመስሉ እንደሚችሉ አዳዲስ ክርክሮችን አስነስቷል።
የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት ከሆነ ይህ ፈጣን ለውጥ አሜሪካ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር የምታደርገውን ግንኙነት እንደገና ለመፈተሽ እና የራሷን ጥቅም ይበልጥ በሚያስከብር መልኩ ለመቅረጽ የምታደርገው ጥረት መጀመሪያ ሊሆን ይችላል።
