በኢትዮጵያ ባለፉት ስድስት ወራት በተከናወነ የአይን ብሌን ንቅለ ተከላ 184 አይነ ስውራን ብርሃን ማግኘት መቻላቸውን የኢትዮጵያ ደም እና ህብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት ገለጸ።
የባንኩ ስትራቴጂክ ጉዳዮች መሪ ስራ አስፈፃሚ ገብረአብ ፍሰሃ ለትርታ እንደገለጹት፤ ተቋሙ በግማሽ ዓመቱ 225 የአይን ብሌኖችን ለመሰብሰብ አቅዶ፣ 247 ማሰባሰብ ችሏል።
ከእነዚህም ውስጥ 236ቱ በአዲስ አበባ ሲሰበሰቡ፣ ቀሪዎቹ 11 ብሌኖች ደግሞ በጅማ ከተማ የተገኙ ናቸው።
ከተሰበሰቡት 247 ብሌኖች መካከል 184ቱ ከተላላፊ በሽታዎች ነፃ መሆናቸው ተረጋግጦ ለተለያዩ ሆስፒታሎች ተሰራጭተዋል።
በዚህም ለዓመታት በጨለማ ውስጥ የነበሩ 184 ዜጎች የንቅለ ተከላ ህክምና ተደርጎላቸው ዳግም ማየት መቻላቸው ተገልጿል።
ይሁን እንጂ በክልል ከተሞች የአይን ብሌን መውሰድ የሚችሉ ሆስፒታሎች ባለመኖራቸው፣ በአቅርቦትና በፍላጎት መካከል ሰፊ ክፍተት መኖሩን ስራ አስፈፃሚው ጠቁመዋል።
በቀጣይም በየክልሎቹ የሚገኙ ሆስፒታሎች ብሌን የመረከብ አቅም እንዲኖራቸው ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራ ተመላክቷል።
በሌላ በኩል፣ ህብረተሰቡ እያሳየ ያለው የበጎ ፈቃደኝነት ተነሳሽነት እየጨመረ መምጣቱ የተገለጸ ሲሆን፤ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 1,700 ሰዎች ከህልፈታቸው በኋላ የአይን ብሌናቸውን ለመስጠት ቃል መግባታቸውም ታውቋል።
ትርታ ሬድዮ
