ግንባታቸው ያልተጠናቀቀ ጅምር ሕንጻዎች በበጀት እጥረት ምክንያት የግንባታ ሥራቸው እንዳይቋረጥ በገደብ በሚሰጥ ፈቃድ ግንባታቸው ሳይስተጓጎል አገልግሎት እንዲሰጡ የሚፈቅድ ደንብ እና መመሪያ ቢኖርም፤ ከተገቢው የመንግሥት ተቋም ፈቃድ ሳይሰጣቸው የኪራይ አገልግሎት ሲሰጡ የተገኙ 251 ሕንጻዎች ላይ እርምጃ መወሰዱን የአዲስ አበባ ግንባታ ፈቃድ እና ቁጥጥር ባለስልጣን አስታውቋል።
የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር አበበ እሸቱ፤ ጅምር ሕንጻዎች ግንባታቸው ባይጠናቀቅም ተገልጋዮች ላይ ጉዳት በማያስከትል መልኩ ለኪራይ አገልግሎት እንዲውሉ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውሳኔ መተላለፉን አስታውሰዋል።
“ከውሳኔው በኋላ የደህንነት ችግር እንደሌለባቸው የተረጋገጠ በግንባታ ላይ የሚገኙ ሕንጻዎች በየዓመቱ የሚታደስ የመጠቀሚያ ፍቃድ እየተሰጣቸው በኪራይ ገቢ የሕንጻውን ግንባታ የሚያጠናቅቁበት እድል ቢመቻችም፤ ያለምንም ፈቃድ በሚያከራዩት ላይ እርምጃ ተወስዷል” ብለዋል።
አስተዳደራዊ እርምጃ ከተወሰደባቸው 251 ሕንጻዎች መካከል 161 ሕንጻዎች ማስጠንቀቂያ እና የገንዘብ መቀጮ ተቀጥተው አገልግሎታቸውን እንዲቀጥሉ ስለመደረጉ አንስተዋል።
በጅምር ላይ ለሚገኙ ግንባታቸው ያልተጠናቀቀ ሕንጻዎች የመጠቀሚያ ፈቃድ የሚሰጠው በማኅብረተሰቡ ላይ ጉዳት እንደማይደርስ ከተረጋገጠ በኋላ መሆኑን ተናግረዋል።
“ለሁሉም ያልተጠናቀቁ ሕንጻዎች የመከራየት ፈቃድ አይሰጥም” ያሉት ኢንጂነር አበበ፤ ደንብ እና መመሪያውን በመተላለፍ ያለ ፈቃድ የሚያከራዩ የሕንጻ ባለቤቶች ላይ እርምጃ መውሰዱ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።
አሐዱ ሬዲዮ
