ሎሬት ሙላቱ አስታጥቄ ሕንጻ

Date:

የጎንደር ዩንቨርሲቲ ሴኔት ሐምሌ 24 ቀን 2017ዓ.ም ባካሄደው ጉባዔ ሎሬት ሙላቱ አስታጥቄ ላበረከተው ፈርጀ ብዙና ፈር ቀዳጅ የሙያ አስተዋጽዖ የሙዚቃ ትምህርት ቤቱን ሕንጻ “” ብሎ ሰይሞታል።

◾️ሎሬት ሙላቱ አስታጥቄ

በሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ጉልህ አሻራ ካሳረፉ ባለውለታዎች መካከል ኢትዮጵያዊው ሎሬት ሙላቱ አስታጥቄ በግምባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። በ1936 ዓ.ም በጅማ ከተማ የተወለደው አንጋፋው አርቲስት ሙላቱ አስታጥቄ የኢትዮጵያን ባህላዊ ሙዚቃ ከጃዝ እና ላቲን ሙዚቃ ጋር በማስተጋበር ልዩ የሆነ የሙዚቃ ቀለም በመፍጠር የኢትዮጵያ ሙዚቃን ከፍ ያለ እውቅና እንዲያገኝ እና ኢትዮጵያን በዓለም አደባባይ ያስተዋወቀ የአገር ባለውለታ ነው። በዚህም ምክንያት “የኢትዮ-ጃዝ አባት” ተብሎ ይጠራል።

ለንደን፣ ኒውዮርክ እና ቦስተን በሚገኙ ስመጥር የሙዚቃ ትምህርት ቤቶች ተምሯል። በሙያው ብቁ በሆኑ ባለሙያዎች ሰልጥኗል። ጥበብና ክህሎቱን በትምህርት ካዳበረ በኃላ “Broken Flowers“ ለተሰኘው የእንግሊዝኛ ፊልም ማጀቢያ ሙዚቃ መሥራት ጨምሮ ታላላቅ አገራዊና ዓለም ዓቀፋዊ መድረኮች ላይ ሥራውን አቅርቧል።

በዘመን ተሻጋሪ የጥበብ ሥራዎቹ የሀገራችንን ውብ የብሔር ብሔረሰቦች ሙዚቃ መሳሪያዎችና ውዝዋዜዎች የዓለም ትኩረት እንዲያገኙ ከማድረግ ባለፈ በታዋቂ አርቲስቶች ሥራዎች ላይ ጭምር እንዲካተቱ ከፍተኛ ተጽእኖ ማሳደር ችሏል። በዓለም ላይ ያሉ ብዙ የጥበብ ሰዎች እርሱ መድረክ ሥራ ላይ ይዟቸው ከቀረቡ የብሔረሰቦቻችን ሙዚቃ፣ ሙዚቃ መሳሪያ እና ውዝዋዜ አያሌ ትምህርቶችን እንደቀሰሙ ይነገራል።

ይህ ጉምቱ የጥበብ ሰው የኢትዮጵያ መንፈሳዊ ዜማ እና መሳሪያዎችን ለትውልድ ለማስተማርና ለማሳደግ ያላሰለሰ ጥረት አድርጓል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎች ታሪካዊ ሚና እና በሀገሪቱ የሙዚቃ ቅርስ ላይ ያላቸውን ተፅእኖ የሚዳስስ መጽሐፍም አዘጋጅቷል።

ሎሬት ሙላቱ ለዓለም ሙዚቃ ላበረከተው ታላቅ አስተዋጽኦ በኢትዮጵያ ብሎም በዓለም አቀፍ ደረጃ በርካታ ሽልማቶች ተበርክቶለታል። ከጅማ ዩንቨርስቲ የክብር ዶክትሬት እንዲሁም የህይወት ዘመን የክብር ሽልማት ተሸላሚ፤ ከበርክሌይ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ያገኙ የመጀመሪያው ጥቁር አፍሪካዊ፤ በጀርመን አገር በስሙ መንገድ የተሰየመለት፤ በፈረንሳይ መንግሥት የአገሪቱ ከፍተኛ የክብር ኒሻን “Ordre des Arts et des Lettres” ተሸላሚ፤ እንዲሁም ከኢጣልያ መንግሥትም ‘Ordine della Stella d’Italia’ ኒሻን ከተበረከቱለት እውቅናዎችና ሽልማቶች ከብዙ በጥቂቱ ይጠቀሳሉ።

በጎንደር ዩኒቨርሲቲም በተለያዩ ጊዚያት በተጋባዥነት እየተገኘ የሙዚቃ ትምህርት ክፍሉ እንዲጠናከር ልምድና እውቀቱን ለመምህራንና ተማሪዎች አካፍሏል።

ስለሆነም የጎንደር ዩንቨርሲቲ ሴኔት ሐምሌ 24 ቀን 2017ዓ.ም ባካሄደው ጉባዔ ሎሬት ሙላቱ አስታጥቄ ላበረከተው ፈርጀ ብዙና ፈር ቀዳጅ የሙያ አስተዋጽዖ እውቅና ለመስጠትና ትውልዱ እንዲማሩበት በማሰብ የሙዚቃ ትምህርት ቤቱን ሕንጻ “” ብሎ ሰይሞታል።

ያጋሩ!

መጽሔቶች

በብዛት የተነበቡ

ተጨማሪ ጽሑፎች
ተመሳሳይ

የተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጂ ዑመር ኢድሪስ ሥርዓተ ቀብር ተፈጸመ

የተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጂ ዑመር ኢድሪስ ሥርዓተ ቀብር ተፈጽሟል፡፡ በሥርዓተ...

የተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጂ ዑመር ኢድሪስ አስክሬን ሽኝት በሚሊንዬም አዳራሽ ተካሂዷል

የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ታየ አጽቀስላሴ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክርቤት...

ሸህ ዑመር ገነቴ!!!

እንዲህ ወደ ደገር…እንዲህ ወደ ገታ…ደግሞም ወደ ዳና፤ጫሌ ገንደጎራ፤የተሰየማችሁ፤ሰው መሆን…..ሰው...