የ28 ዓመቷ ወይዘሮ ሰናይት ታምራት ቀደም ሲል በነበረው እርግዝናዋ በተፈጠረባት የሾተላይ ችግር ምክንያት በሁለተኛው እርግዝና ‘ዳግም ልጄን አጣው ይሆን’ የሚል ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ በመግባቷ፤ ከ21ኛ ሳምንቷ ጀምሮ የሕክምና ክትትሏ ከፍ እንዲል ተደርጎ ነበር፡፡
የ21 ሳምንት ብቻ ዕድሜ የነበረው ፅንሱ በማህፀን ውስጥ እንዳለ የደም ማነስ ችግር ስላጋጠመው፤ ሕክምናው እጅግ ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ ተከናውኗል፡፡
እናት የመጀመሪያዎቹን ወራቶች በሳምት ሁለት ቀን ለክትትል ወደ ሕክምና ተቋም በማምራት አስፈላጊውን ክትትል በማድረጓ ፅንሱ መፋፋት እና እድገት ማሳየት መቻሉም ተጠቁሟል፡፡
ለእናት እና ለልጅ ጥብቅ የሆነ ክትትል በማድረግ ደም የመለገስ ሂደቱ 10 ጊዜ ቀጥሎ፤ ፅንሱ የመወለጃው ጊዜ ሲደርስ በቀዶ ሕክምና 3.5 ኪ.ግ የሚመዝን ሕጻን በሰላም ተገላግላ እናት ልጇን ማቀፍ መቻሏ ተነግሯል ፡፡
በየካቲት 12 ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ አበበች ጎበና እናቶች እና ህፃናት ሕክምና ማዕከል በትናንትናው እለት የተፈጠረው ይህ ክስተት፤ ከብራዚል በመቀጠል በዓለም ሁለተኛው በአፍሪካ ደግሞ የመጀመሪያው መሆን እንደቻለ ተዘግቧል፡፡
