የሕንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ የሩሲያን ነዳጅ ላለመግዛት መስማማታቸውን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ትናንት ነበር የተናገሩት፡፡
ህንድ በበኩሏ የአሜሪካዉ ፕሬዝዳንት የሩስያን ዘይት ወደ ሀገር ውስጥ ማስገባት ለማቆም ተስማምታለች ሲሉ የሰጡትን አስተያየት ተቃዉማለች፡፡
ይህም ምናልባት ግንኙነታቸዉን ያሻከረ እና በቅርቡ እልባት ያገኛል ተብሎ የማይታሰብ ጉዳይ ነዉ ተብሏል፡፡
ትራምፕ ትናንት ባደረጉት ንግግር፤ ሕንድ “በአጭር ጊዜ ውስጥ” ከሩሲያ ነዳጅ መግዛት እንደምታቆም ከሞዲ ማረጋገጫ ማግኘታቸውን እና ይህም ‘ትልቅ እቀባ’ መሆኑን ገልጸዋል።
የአገሪቷ መንግሥት ቃል አቀባይ ለትራምፕ ንግግር በሰጡት ምላሽም ” ከሕንድ ጋር የኢነርጂ ትብብሩን ለማጠናከር ፍላጎት ካሳየው የአሜሪካ አስተዳደር ጋር ውይይቶች እየተካሄዱ ነው” ብለዋል።
ነገር ግን ሐሙስ ዕለት የሕንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ራንዲር ጃይስዋል ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፤ በትራምፕ እና በሞዲ መካከል “ምንም ዓይነት የተደረገ ውይይት መኖሩን አላውቅም” ያሉ ሲሆን፤ የሕንድ መንግስት ከሩሲያ ዘይት መግዛቱን ለማቆሙ ምንም ዓይነት ማረጋገጫ እንደሌላቸው ተናግረዋል።
ህንድ ከክሬምሊን ጋር የጠበቀ ግኑኝነት ያላት ሲሆን፤ በዚህ ዓመት መጨረሻ ላይ የሩሲያውን ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲንን ተቀብላ ታስተናግዳለች።
በ2022 ሩሲያ ዩክሬንን ከወረረች በኋላም ከሞስኮ ከፍተኛ የነዳጅ ገዢዎች አንዷ ሆና ብቅ ብላለች።
ጦርነቱ በሞስኮ የነዳጅ ኢንዱስትሪ ላይ ከፍተኛ ማዕቀብ ያስከተለ ሲሆን፤ ዋጋዎችንም አሽቆልቁሏል።
አሜሪካ የዩክሬንን ጦርነት ለማስቆም የሚደረጉት ጥረቶች አካል በማድረግ በክሬሚሊን ላይ የኢኮኖሚ ጫናዎችን ማሳደር ትፈልጋለች።
የአሜሪካው ፕሬዚደንት ሕንድ ከሩሲያ ነዳጅ መግዛቷን ለማስቆም ቢፈልጉም፤ደልሒ ግን እስካሁን ይህንን ሳትቀበል ቆይታለች ሲል ሲ ኤን ኤን ዘግቧል።