ኢትዮጵያ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና (AfCFTA) ስምምነትን በይፋ ለመተግበር የሚያስችል ደንብ ማውጣቷን አስታውቃለች።
በሚኒስትሮች ምክር ቤት የወጣው ደንብ ቁጥር 574/2017፣ ከአባል ሀገራት ወደ ኢትዮጵያ በሚገቡ ዕቃዎች ላይ የሚደረገውን የጉምሩክ ቀረጥ ቅነሳ በዝርዝር አስቀምጧል።
በነጋሪት ጋዜጣ በታተመዉ ደንብ መሰረት፣ ዕቃዎች በሶስት ምድቦች የተከፈሉ ሲሆን፣ ከ90% በላይ የሚሆኑት ዕቃዎች በ10 ዓመታት ውስጥ ቀስ በቀስ እየቀነሱ በመሄድ ሙሉ በሙሉ ከቀረጥ ነፃ ይሆናሉ። ሌላኛው የምድብ “ለ” ዕቃዎች ከ7% አይበልጡም፣ እነሱም ከ2026 ጀምሮ በ8 ዓመታት ውስጥ ከቀረጥ ነፃ ይሆናሉ።
የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጠና ታሪፍ ሰንጠረዥ ተፈጻሚ የሚሆንባቸውን አባል ሀገራት የሚገልጽ ሲሆን፣ የገንዘብ ሚኒስቴር ደግሞ የዕቃዎችን ምድብ የመለየት እና የማስተካከል ስልጣን ተሰጥቶታል። በተጨማሪም፣ የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ለዕቃዎች የሥሪት ሀገር የምስክር ወረቀት ይሰጣል።
ይህ ደንብ ከነሐሴ 2017 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ የተደረገ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ንግድ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጋር ይበልጥ እንዲቀላቀል እና አዲስ የንግድ እድሎችን እንዲፈጥር ይጠበቃል ሲል ካፒታል አስነብቧል።