በአዲስ አበባ ታሪካዊ የአፍሪካ አዳራሽ ይፋ በተደረገው አዲስ የአፍሪካ ምርጥ ብራንዶች ሪፖርት መሰረት፣ ቻይና በኢትዮጵያ ውስጥ እጅግ ተወዳጅ ሀገር በመሆን ኢትዮጵያን እራሷን ጭምር በልጣለች። ይህ ጥናት የውጭ ሀገራት ተፅዕኖን እና የሀገር ውስጥ ብራንዶች የሚያጋጥሟቸውን ተግዳሮቶች የሚያመላክት ነዉ ተብሏል።
በ31 ሀገራት በተካሄደው የብራንድ አፍሪካ ጥናት፣ ኢትዮጵያውያን ከሚያደንቋቸው ሀገራት ዝርዝር ውስጥ ቻይና ቀዳሚ ስትሆን፣ ኢትዮጵያ፣ ሩሲያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ እና የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ይከተሏታል።
ምንም እንኳን 68% የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን ለአፍሪካ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ብሩህ ተስፋ ቢኖራቸውም፣ የሀገር ውስጥ ብራንዶች ግን እውቅና ለማግኘት እየተቸገሩ ነው።
በኢትዮጵያ ከሚደነቁ 100 ምርጥ ብራንዶች ውስጥ 6% ብቻ ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ፣ በአጠቃላይ ከሚደነቁ ብራንዶች ውስጥ 13% ብቻ የሀገር ውስጥ ናቸው። ይህ የውጭ ብራንዶች የበላይነትን እና የሀገር ውስጥ ኩባንያዎች ተጨማሪ ትኩረት እንደሚያስፈልጋቸው ያሳያል።
በአፍሪካ Nike፣ Adidas፣ Samsung፣ Coca-Cola እና Apple ከፍተኛ አምስት ተወዳጅ ብራንዶች ሲሆኑ፣ በኢትዮጵያ ደግሞ መቄዶኒያ፣ ኢትዮ ቴሌኮም እና ኮካ ኮላ “ለህብረተሰብ መልካም በመስራት” ተወዳጅነትን አግኝተዋል።