የአዲስ አበባ ከተማ የመንግስት ንብረት አስተዳደር ባለስልጣን፤ ኤሌክትሮኒክስና ፈርኒቸሮችን መልሼ በመጠገን ከ187 ሚሊየን ብር በላይ ከብክነት አድኛለሁ ብሏል።
ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ባለፈው የ2017 በጀት ዓመት 5,580 ፈርኒቸሮችንና 6,519 የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎችን ጠግኖ ወደ አግልግሎት መመለሱን ተናግሯል።
ይህ የተነገረው የኤሌክትሮኒክስና የፈርኒቸር ጥገና የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ ነው።
የባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የንብረት ዘርፍ ም/ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ጸሐይ መንግስቱ ያለ አገልግሎት የተከማቹ ንብረቶችን በወቅቱ በማስወገድና በመጠገን ብክነትን መከላከል ያስፈልጋል ብለዋል።
ኃላፊዋ ለ2018 በጀት ዓመትም ተጠግነው አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ንብረቶች በኮሌጅ፣ በሆስፒታል፣ በጤና ጣቢያ፣ በትምህርት ቤት ወረዳ እና ክፍለ ከተማ፣ የመለየት ስራ ጨርሰናል ብለዋል።
በአንድ ወቅት ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አህመድ በህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ተገኝተው ንግግር ሲያደርጉ ይህንኑ ሃሳብ አንስተው እንደነር ይታወሳል።
በየመንግስት ተቋማቱ ተከማችተው የሚገኙ ንብረቶችን ጠግኖ ሥራ ላይ በማዋል አለያም በመሸጥ ከፍተኛ ገቢ ማግኘት ይቻላል ብለው ነበር።
ንጋት መኮንን ( ሽገር 102.1)