በኢትዮጵያ ለሚገኙ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከሀገር ውስጥ የሚቀርበው ግብዓት ከ5 በመቶ የማይበልጥ መሆኑን የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ያካሄደው ጥናት ማረጋገጡን ገለጸ።
የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት የኢንዱስትሪ ልማት ተመራማሪ ሲሳይ ስንታየሁ (ዶ/ር) ኢንስቲትዩቱ ባደረገው ጥናት 95 በመቶ የሚሆኑት በኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ያሉ ፋብሪካዎች የሚጠቀሙት ግብዓት ከሀገር ውጭ የሚገባ መሆኑ ተረጋግጧል ብለዋል።
ይህም ፓርኮቹ እንዲያመነጩ የሚፈለገውን ያህል የውጭ ምንዛሬና ሀብት እንዳያመነጩ ዋነኛ እንቅፋት ሆኖባቸዋል ሲሉ ሲሳይ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
በሀገር ውስጥ የሚመረቱ ጥሬ ዕቃዎች የጥራት ጉድለት እንዲሁም ምርቶቹን ወደ ፓርኮች ለመውሰድ የሚኖረው የትራንስፖርትና የሎጀስቲክስ ችግር ፋብሪካዎቹ የሀገር ውስጥ ምርቶችን እንዳይመርጡ ምክንያት መሆኑን ተመራማሪው ጠቁመዋል።
ለዚህም መፍትሔ ይሆን ዘንድ መንግሥት የሀገር ውስጥ ጥሬ ዕቃዎች በጥራት እንዲመረቱ ማገዝ፣ ሎጀስቲክሱን ማዘመን እንዲሁም የሀገር ውስጥ ጥሬ ዕቃ የሚጠቀሙ ባለሀብቶችን ማበረታታት እንደሚገባው ገልጸዋል።
በተጨማሪም የሀገር ውስጥ ፋብሪካዎች ከውጭ ፋብሪካዎች ጋር በጥምረት እንዲሠሩ ማበረታታት አስፈላጊ መሆኑን ተመራማሪው አብራርተዋል።
