ከ400 በላይ ፍልስጤማውያን መገደላቸው ሪፖርት የተደረገበትን የጋዛ ጥቃት ገና የመጀመሪያው እንደሆነ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ተናገሩ።
እስራኤል በጋዛ ሰርጥ በሐማስ ላይ “ውጊያዋን በሙሉ ኃይል ጀምራለች” ሲሉ ኔታንያሁ አስጠንቅቀዋል፡፡
ጥር ወር ላይ ከተደረሰው የጋዛ የተኩስ አቁም ስምምነት በኋላ እስራኤል የፈጸመችው ከባዱ የአየር ጥቃት ነው ተብሏል።
ጥቃቱ በተፈጸመበት ወቅት በርካቶች ለረመዳን ጾም የቀኑን የመጨረሻ ምግባቸውን እየበሉ እንደነበር የዓይን እማኞች ተናግረዋል።
በቦታው አስከሬኖች ወዳድቀው፣ የቆሰሉ ሰዎች ህክምና ለማግኘት እየተማጸኑ እንዲሁም እሳት ተቀጣጥሎ የነበረ ሲሆን፤ ሁኔታውንም አሰቃቂ ብለውታል።
ኔታንያሁ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት “ድርድሩ የሚቀጥለው በእሳት ውስጥ ብቻ ነው፤ ይህም ገና ጅምር ነው” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ አስተያየት የተሰማው የእስራኤል ጦር በጋዛ የሃማስ ይዞታዎች ናቸው በሚል ከፍተኛ የአየር ጥቃት ከከፈተ በኋላ ነው።
የጋዛ የጤና ሚኒስቴር በዚህ ጥቃት ከ400 በላይ ሰዎች መገደላቸውን እንዲሁም በመቶዎች የሚቆጠሩ መቁሰላቸውን አስታውቋል።
የተኩስ አቁሙ አሸማጋይ የሆነችው ግብጽ ይህንን የእስራኤል ጥቃት በጽኑ አውግዛለች።
