የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝደንት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ በተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጂ ዑመር ኢድሪስ ወደ አኼራ መሄድ የተሰማቸውን ጥልቅ ሀዘን ገልፀዋል።
የቀድሞው የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝደንት ተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጅ ዑመር ኢድሪስ በዲን እውቀታቸው አንቱ የተሰኙ በመንፈሳዊ አገልግሎታቸውም ላቅ ያለ ደረጃ የነበራቸው ናቸው ያሉት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ፤ እሳቸውን ማጣት እጅግ ከባድ ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ህጋዊ ሰውነት እንዲያገኝ፣ እስላማዊ ባንኮች እንዲቋቋሙ የሰሩት ታላቅ ስራ በታሪክ ሲታወስ ይኖራል ያሉት ሸይኽ ሐጂ ኢብራሂም ቱፋ፤ የሙስሊሙ አንድነት እንዲጠናከር እድሜ ዘመናቸውን መልፋታቸውን ገልፀዋል።
በዚህ ረገድ ተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጂ ዑመር ኢድሪስ ላበረከቱት ሁሉ ጠቅላይ ምክር ቤቱ ከፍተኛ ክብር እና እውቅና ይሰጣል ብለዋል፡፡
ለሀገራችን ሙስሉም የከፈሉት ዋጋ እና ያበረከቱት አስተዋፅኦ መቼም አይዘነጋም ያሉት ፕሬዝደንቱ፤ መልካም ስራቸውን ሁሉ አሏህ እንዲቀበላቸው ምንዳቸውንም ጀነተል ፊርደውስ እንዲያደርግላቸው አሏህን እንለምናለን፣ በያለንበት ዱዓ እናድርግላቸዋለን ሲሉ ገልጸዋል።
የቀብር ስነ-ስርዐቱ የታላቁን ዐሊም ክብር በሚመጥን እስላማዊ አደብ፣ በመንግስት ደረጃም ጭምር እንዲፈፀም ሀገራዊ ኮሚቴ እንደሚቋቋም እና አጠቃላይ ሁኔታው ይፋ እንደሚደረግ ፕሬዝደንቱ አስታውቀዋል።