የኮንግረስ አባል ኢልሀን ኡመርና የፕሬዝደንት ትራምፕ ውዝግብ እንደቀጠለ ነው፡፡ ፕሬዝደንት ትራምፕ ሀሙስ እለት በሰጡት መግለጫ የሱማሊያውን ፕሬዝደንት ሀሰን ሼክ መሀሙድን አግኝተው በእሷ ጉዳይ ማነጋገራቸውን ገልፀው ነበር፡፡
በንግግራቸው ወቅትም ‹‹እኔ ኢልሀንን ወደ ሱማሊያ ላባርራት ነው›› የሚል ሀሳብ አቅርበው የሱማሊያው ፕሬዝደንት እንደሚቀበሏት መጠየቃቸውን ተናግረዋል፡፡
የሱማሊያው ፕሬዝደንት ግን ‹‹አልፈልጋትም ብሎኛል›› በማለት በመግለጫቸው ላይ አስታውቀዋል፡፡ ለዚህ ንግግር የ42 አመቷ የዲሞክራት አባል የሆነችው ኢልሀን ኡመር በኤክስ ገጿ ላይ ዛሬ መልስ ሰጥታለች፡፡
በምላሿም ትራምፕ ከዚህ ቀደም ሱማሊያ ፕሬዝደንት የሌላት አድርገው መናገራቸውን አውስታ አሁን ደግሞ የፈጠራ ወሬ መንዛታቸውን አስረድታለች፡፡
ጨምራም ‹‹ሱማሊያ ፕሬዝደንት እንዳላት ከመካድ አንስቶ የሌለ ታሪክ እስከመፍጠር ድረስ ትራምፕ ውሸታም ናቸው፡፡ የእኚህን ሰው አሳፋሪና የጅል ንግግር ማንም ከቁም ነገር ሊቆጥረው አይገባም›› ብላለች፡፡
ፕሬዝደንት ትራምፕ በዚህች የኮንግረስ አባል ላይ እንዲህ አይነት ከባድ አስተያየት ሲሰጡ በአንድ ሳምንት ይህ ሁለተኛ ጊዜያቸው ነው፡፡
በኢልሀን ኡመርና በትራምፕ መካከል ውዝግብ ሊነሳ የቻለው በአክቲቪስት ቻርሊ ኪርክ ግድያ ላይ በተሰጠችው አስተያየት እንደሆነ ከዚህ ቀደም መዘገባችን ይታወሳል፡፡