የኢራን ጠቅላይ መሪነት ሥልጣንን ከተረከቡ ወዲህ በአካል ያልታዩት ሞጅታባ ኻሜኒ፤ አባታቸውን በገደለው የአየር ጥቃት ከደረሰባቸው የፊት እና የእግር ጉዳት እያገገሙ እንደሆነ በቅርባቸው ካሉ ምንጮች መስማቱን ሮይተርስ ዘገበ።
የዜና ወኪሉ ዘገባ እንደሚያመለክተው አዲሱ ጠቅላይ መሪ በጥቃቱ ፊታቸው እንደተበላሸ እና አንድ ወይም ሁለት እግሮቻቸው ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰ ሦስት ምንጮች ተናግረዋል።
ይህም ቢሆን ግን የ56 ዓመቱ ሞጅታባ ከጉዳታቸው እያገገሙ እንደሆነ እና አዕምሯቸው ስል ሆኖ መቀጠሉን ምንጮቹ ገልጸዋል ተብሏል።በድምጽ በሚደረጉ የኦንላይን ስብስብሰባዎች ላይ እየተሳተፉ እንዲሁም ከአሜሪካ ጋር እንደሚሄደው ድርድር ባሉ ዋነኛ ጉዳዮች ላይ ውሳኔ እየሰጡ መሆኑ ተገልጿል።
በጦርነቱ የመጀመሪያ ቀን በተፈጸመው ጥቃት የተገደሉት አባታቸውን ተክተው ወደ ሥልጣን የመጡት ሞጅታባ ኻሜኒ፤ በዚሁ ዕለት የደረሰባቸው ጉዳት መጠን እስካሁን በይፋ አልተገለጸም።
ከዚህ ቀደም የኢራን መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ በጦርነት ከፍተኛ ጉዳት ለደረሰባቸው ሰዎች ጥቅም ላይ የሚውልን ቃል በመጠቀም ያሉበት ሁኔታ ጠቁሞ ነበር።
የአሜሪካው መከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴት በበኩላቸው ኻሜኒ “መቁሰላቸውን እና አካል መጉደል ደርሶባቸው ሊሆን እንደሚችል” ባለፈው ወር ተናግረው ነበር።የአሜሪካ የስለላ መረጃ ግን ኻሜኒ እግራቸውን አጥተዋል ተብሎ እንደሚታመን ማሳየቱን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጭ መናገራቸውን የሮይተርስ ዘገባ ያመለክታል።
