ለብፁዕ ቅዱስ አባታችን አቡነ ኤልያስ
የአርባ ምንጭ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ።
ብፁዕነትዎ በአባትነት ስልጣንዎ “ለዶ/ር ወዳጄነህ አድርሱልኝ” ብለው ያስተላለፉልኝ መልዕክት ደርሶኛል። ብዙ ሰዎች ቪዲዬውን እየላኩልኝ ደጋግሜ አየሁት፣ ሰማሁት።
በመጀመርያ የእኔ ከንቱ ስሞ በእርስዎ ቅዱስ አንደበት በመጠራቱ ብቻ እግዚአብሔርን አመሰግኛለሁ ። እርስዎ ለእኔ ብለው ተናገሩ፣ ጥሪ አቀረቡልኝ እንጂ ያለዚያማ የእኔ አይነቱ ሀጢያተኛ ወደ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቢመጣ ተጨማሪ ሸክም ቢሆንባት እንጂ እርሷን ምን ሊጠቅማት?
ብፁዕ አባታችን! እርስዎ ጥሪውን ያቀረቡበት የእግዚአብሔር ፍቅር ልብ የሚነካ ነበር። እንዲህ እንደርስዎ መለኮታዊ ፍቅር ያደረባችው አባቶች ቢበዙልን ምድራችን ትፈወስ ነበር ብዬ አምናለሁ። ያቀረቡልኝን ጥሪ፣ የመከሩኝን ምክር ስሜታዊ ሳልሆን ከልቤ፣ በፅሞና እንደማስብበት፣ እንደምፀልይበት ቃል እገባሎታለሁ።
እንግዲህ መልዕክትዎ ደጋግሞ ቢደርሰኝ ይቺን ትንሽ ፅሁፍ ልፅፍሎት ደፈርኩኝ።
ይቅር ይበሉኝ።
እግዚአብሔር ይስጥልኝ!
ውለታዎንም ይክፈልልኝ!
ዶ/ር ወዳጄነህ መሐረነ።
(ከዚህ ጋ በተገናኘም ባልተገናኘም መንገድ የተሳሳተ መረጃ የምታቀርቡ አንዳንድ ሚዲያዎች ብትታረሙ መልካም ይመስለኛል።
አንድ ሰው ታዋቂ ሆነ አልሆነ፣ ተማረ አልተማረ ወደ ቤተክርስትያን መምጣቱ፣ መመለሱ ጥቅሙ ለእሱው ነው እንጂ ለንፅህት፣ ቅድስት ቤተ ክርስትያን የሚጨምርላት አንዳች ነገር የለም።
“እከሌ ወደዚህ ተመለሰ” በሚል ያልተረጋገጠ ዜና እግዚአብሔር አይከብርም፣ ሀይማኖትም አይጠቀምም።)