በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ በመስራት ከ30 አመት በላይ ልምድ ያካበተው ጋዜጠኛ አብዱል ሰመድ መሀመድ በአዲስ አበባ ከመንገድ ላይ ታፍኖ መወሰዱን ቤተሰቦቹ ገለፁ፡፡
ጋዜጠኛው ሰኞ እለት ነሀሴ 5 ቀን 2017 ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች በመኪና እንደተወሰደ ተገልጿል፡፡
ቤተሰቦቹ ከዚያን እለት አንስቶ በአዲስ አበባ ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎችና ሜክሲኮ በሚገኘው ፌዴራል ፖሊስ እስር ቤት ጭምር ቢፈልጉትም ሊያገኙት እንዳልቻሉ አስረድተዋል፡፡
በኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ውስጥ ለረጀም አመታት ያገለገለው ጋዜጠኛ አብዱል ሰመድ መሀመድ በአሁኑ ወቅት በአሀዱ ሬዲዮ በሚተላለፈው ቅዳሜ ገበያ ፕሮግራም ላይ የሚሰራ ሲሆን በተለያዩ የዩቲዩብ ገፆች ላይ በድምፁ ዝግጅቶችን በማንበብ የሚሰራ ነው፡፡
የጋዜጠኛው ቤተሰቦች ለዘ-ሐበሻ ሲናገሩ ‹‹ያልፈለግንበት ቦታ የለም፡፡ ከጠፋ ዛሬ 6ተኛ ቀኑ በመሆኑ የደህንነቱ ጉዳይ አሳስቦናል›› ብለዋል፡፡ ለአለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴና ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ጉዳዩን አሳውቀው ውጤቱን በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውንም ከድሬ ቲዩብ ተመልክተናል።
የሪፖርተር ጋዜጣ ባልደረባ የሆነው ጋዜጠኛ ዮናስ አማረ “ባልታወቁና ጭምብል ባደረጉ ሰዎች” ከሚኖርበት ከሸገር ከተማ ኮዬ ፈጬ ኮንዶሚኒዬም ረቡዕ ነሐሴ 7 ቀን 2017 ዓ.ም ምሽት ላይ መወሰዱን የአከባቢው የጥበቃ ሰራተኞች ነገሩኝ ብሎ ሪፖርተር ጋዜጣ አስታውቋል።
ጋዜጠኛ ዮናስ አማረ ላለፉት አራት ቀናት ማለትም ከነሐሴ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሥራ ባለመግባቱ በእጅ ስልኩ ላይ ቢደወልለትም ሆነ ከቤተሰቦቹ ለማጣራት ቢሞከርም ማግኘት አለመቻሉም ተጠቁሟል።
ጋዜጠኛውን እነማን እንደወሰዱትና የት እንደተወሰደ እስከ አሁን ድረስ ማወቅ አልተቻለም ተብሏል።