የገንዘብ ሚኒስቴር፣ የደረጃ “ሀ” ግብር ከፋዮች የቅድሚያ ግብር ክፍያ ጊዜን አስመልክቶ አዲስ ማብራሪያ ሰጥቷል። ሚኒስቴሩ እንዳስታወቀው፣ የቅድሚያ ግብር የሚከፈለው በየሦስት ወሩ ሲሆን፣ የጊዜው ስሌት የሚጀምረው የሂሳብ ሪፖርት ከቀረበበት ወር ማብቂያ ጀምሮ ነው።
ሚኒስትሩ ለገቢዎች ቢሮ የፃፈዉ ደብዳቤ ላይ ግብር ከፋዮች የየሦስት ወሩን የቅድሚያ ግብር ክፍያ፣ የሂሳብ ሪፖርት ካቀረቡበት ወር በኋላ ባሉት በየሦስት ወሩ መጨረሻ ባሉት 30 ቀናት ውስጥ መፈጸም ይጠበቅባቸዋል።
በዚህ ማብራሪያዉ ላይ እንደጠቆመዉ የሂሳብ ሪፖርታቸውን በጥቅምት ወር የሚያቀርቡ ግብር ከፋዮች፣ የመጀመሪያውን ቅድሚያ ግብር በየካቲት ወር፣ ሁለተኛውን በግንቦት ወር፣ ሦስተኛውን ደግሞ በነሐሴ ወር ይከፍላሉ። በተጨማሪም፣ ዓመታዊ ግብራቸውን አጠቃለው እስከ ጥቅምት ወር መጨረሻ ድረስ መክፈል እንደሚኖርባቸው በዝርዝር አስቀምጧል።
ይህን ተከትሎ የሂሳብ ሪፖርት የሚቀርብበት ወር የግብር ክፍያ ማጠናቀቂያ ወር እንደሚሆን የገለፀ ሲሆን በዚህም መሰረት፣ አንድ ግብር ከፋይ በየሦስት ወሩ የከፈለው ቅድሚያ ግብር ከጠቅላላ ዓመታዊ ግብሩ ያነሰ ከሆነ፣ የቀረውን ልዩነት መክፈል ግዴታ እንዳለበት አፅንኦት ሰጥቷል።
CapitalNews