ተማሪ ሊዛ ደሳለ የተባለች ወጣት ሰሞኑን በደሴ ከተማ “ የአስገድዶ መድፈርና ግድያ ጥቃት ተፈጽሞባት ” መገኘቷ ተሰምቷል፡፡
መረጃዎች እንደሚያመላክቱት ወጣቷ መስከረም 27 ቀን 2018 ዓ/ም ስልኳን ለማሰራት በደሴ ከተማ ወደ ፒያሳ በወጣችበት አልተመለሰችም፡፡
ይህን ተከትሎ ፍለጋ ሲደረግ ግን “ተደፍራና ተገድላ ተገኝታለች” የተባለ ሲሆን፣ “ፍትህ ለተማሪ ሊዛ” የሚል ጥያቄዎች ኢንተርኔቱን አጨናንቀውታል።
ወጣቷ “ የወሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ናት ” የሚሉ መረጃዎች መሰራጨታቸውን ተከትሎ ቲክቫህ ኢትዮጵያ ምላሽ የጠየቃቸው አንድ የዩኒቨርሲቲው አካል ጉዳዩን አጣርተው በሰጡት ምላሽ፣ “ የተማሪዎች አገልግሎት ጋር ደውየ ነበር፤ ‘እንዲህ አይነት ነገር እኛ አልተከሰተም፡፡ ተከሰተ የሚባለውም ከወይዘሮ ስህን ኮሌጅ ነው’ ” እንዳሏቸው ገልጸዋል፡፡
እኝሁ የዩኒቨርሲቲው አካል፣ “የደሴ ካምፓስ ተማሪ አይደለችም፡፡ የወይዘሮ ስህን ኮሌጅ ተማሪ ናት፡፡ የኛ ተማሪ አለመሆኗን አሁን ከተማሪ አገልግሎት ደውዬ አጣርቻለሁ ” ሲሉም አክለዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በማህበራዊ ሚዲያ ስሙ በሀሰት መነሳቱን ገልጾ ይህን ባደረጉት ላይ ተጠያቂነት እንደሚከተል ገልጿል።
በሊዛ ደሳለ ሞት ማዘኑንም ገልጾ ለወዳጅ ዘመዶች መፅናናትን ተመኝቷል።
የተማሪዋን ቤተሰቦች ለማግኘት ያደረገው ጥረት ባይሳከለትም፣ ከቆቦ ከተማ ነዋሪዎች ባደረገው ማጣራት ግን ተማሪ ሊዛ ደሳለ በሰሜን ወሎ ዞን የራያ ቆቦ ወረዳ ቆቦ ከተማ ታዲጊ መሆኗን ለማወቅ ችሏል፡፡
የወይዘሮ ስህን ኮሌጅ ኃላፊዎችን ፣ የደሴ ከተማ ፓሊስን ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ ለጊዜው አልተሳካም።
የደሴ ከተማ ኮሚዩኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ ነስረዲን ኃይሌ፣ ” መድረክ እየመራሁ ነው ” በማለታቸው ሀሳባቸውን ማካተት አልተቻለም። ኃላፊው ቆየተው በላኩት የፅሑፍ መልዕክት ዝርዝር መረጃ ይሰጧችኋል ሲሉ ኮማንደር ሰይድ የሚባሉ አካል ጠቁመዋል።
” ጉዳዩን ተከታትለውታል ” የተባሉት ኮማንደር ሰይድ አሊ ምላሽ ብንጠይቃቸውም፣ “ እኔ አልሰጥም፤ ፖሊስ ነው መግለጫ የሚሰጠው፤ ፖሊስ መምሪያ ኃላፊው ናቸው የሚሰጡት ” ብለዋል።
“ የምርመራ ኬዝ ስለሆነ ጥንቃቄ ያስፈልገዋል ” ያሉት እኝሁ አካል፣ የምርመራውን ሂደት ሳይሆን የግድያውንና ሁነት እንዲያስረዱ ስንጠይቃቸው ማብራሪያ ለመስጠት ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።
@tikvahethiopia