ኢትዮጵያውያን ቤተሰቦችን በአንድ ላይ ለማሰባሰብ ዓላማ በማድረግ ስያሜውን “ቻናል 1” ያለው ቻናል ዋን ቴሌቪዥን ጣቢያ ነሐሴ 18 2017 ዓ.ሞ ከቀኑ 6:00 ጀምሮ “እሁድን አንድ ላይ” በተሰኘ ፕሮግራም መደበኛ ስርጭቱን እንደሚጀምር ኤቨንት አዲስ ሚዲያ ከጣቢያው ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
ጣቢያው ቀደም ብሎ በርካታ ፕሮግራሞችን እያዘጋጀ እንደከረመ እና አዳዲስ የፕሮግራም ይዘቶችን ለተመልካች ይዞ ለመምጣት ዝግጅት ሲያደርግ እንደቆየ ተገልጿል።
ቻናል 1 ወደ መደበኛ ስርጭቱ ሲገባ ከ80 መቶ በላይ አዳዲስ (ኦርጂናል)ይዘት ያላቸው ኢትዮጵያዊ ድራማዎች፣ ኮሚዲዎች፣ ሪያሊቲ ሾዎች፤ጌም ሾዎች፣ ስፖርታዊ ፕሮግራሞች፣ ሙዚቃዎች፣ ትምህርታዊ ፕሮግራሞች፣ የልጆች ዝግጅቶች ለትውልድ በሚመጥን መልኩ የተዘጋጁ ሲሆን ቀሪዎቹ 20 ከመቶ የሚሆኑት ይዘቶችም የኢትዮጵያን ቤተሰብ ባህልና ወግ እና ልምድ ግምት ውስጥ ያስገቡ ፕሮግራምች ናቸው ተብሏል።
በፕሮግራም አቅራቢነት ናፍቆት ትዕግሥቱ፣ሊያ ሳሙኤል፣ ስንታየሁ ብዙነህ እና ሌሎችም በጣቢያው በሚተላለፉ ፕሮግራሞች ላይ እንደሚሳተፉ ተገልጿል።
ቴሌቪዥን ጣቢያው ሙሉ በሙሉ የመዝናኛ ጣቢያው ባይሆንም ዋና ትኩረቱ መዝናኛ እንደሆነም ተነግሯል።
“ቻናል 1” ቴሌቪዥን ጣቢያ ሳምንቱን ሙሉ የ24 ሰዓታት ስርጭት ይኖረዋል ተብሏል።
ጣቢያው በኢትዮ-ሳት ላይ በ11545 H 45000 ፍሪኩዌንሲ ላይ ይገኛል።