በኢትዮጵያ ቅጽበታዊ አደጋ ሲከሰት እና ከአቅም በላይ ሲሆን የአስቸኳይ ጊዜ እወጃ ስርአት ለመዘርጋትና ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ረቂቅ አዋጅ ለምክር ቤቱ ቀርቦ ዛሬ መጋቢት 9 ቀን 2017 ዓ.ም ምክክር እንደተደረገበት ተገለጸ።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 20ኛ መደበኛ ስብሰባ የቀረበው የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ረቂቅ አዋጅ የሚል መጠሪያ ያለው ሲሆን ከአስቸኳይ ግዜ እወጃ ስርአት ከመዘርጋት እና ተግባራዊ ከማድረግ በተጨማሪ ተግባራትነ ያቀፈ ነው ተብሏል።
የሰብአዊ ድጋፍ፣ የዘላቂ ልማት እና የሰላም ግንባታ እቅዶችን ለማስተሳሰር የሚያስችል የተሟላ የህግ ማዕቀፍ ለመዘርጋት እንዲያስችል የተዘጋጀ ረቂቅ አዋጅ መሆኑ ተገልጿል፤ ፤ በሚሉ ድምጽ ለቋሚ ኮሚቴው ለዝርዝር እይታ ተልኳል።
የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር የቅድመ አደጋ፣ የአደጋ ወቅትና ድህረ አደጋ ተግባራትን ውጤታማ ለማድረግ የፌደራልና የክልል አስተዳደር ተቋማት የውስጥ አቅም ለመገንባት ያስችሏልም ተብሏል።
ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ምክር ቤት መቋቋምን የተመለከቱ ድንጋጌዎች እና ስለ ኮሚሽኑ ተግባርና ኃላፊነት የምክር ቤቱ ስልጣንና ተግባራት ዝርዝር መረጃ መያዙ ተጠቁሟል።
ስለፌደራል መሪ ዘርፍ ተቋማት እና የክልል መንግስታት ተግባርና ኃላፊነት፣ ስለአደጋ ተጋላጮችና ተጎጂዎች መብትና ግዴታ እንዲሁም ስለ ኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ምላሽ ፈንድ መቋቋም የሚመለከቱና ሌሎች ድንጋጌዎች መካተታቸውም ታውቋል።
የምክር ቤት አባላትም አዋጁ የሚደረጉ ድጋፎች በተቀናጀ መልኩ እንዲደረጉና ለተጎጂዎች እኩል ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም ከእርዳታ ጠባቂነት በመላቀቅ እራስን ለመቻል አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል ።
ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 16/2017 ሆኖ በሙሉ ድምጽ ለውጭ ግንኙነትና ለሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር እይታ መመራቱን ከምክር ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያሳያል።
