በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሚሰሩ የልማት ሥራዎች ሁሉ ኪነ ጥበብ አበይት የትኩረት አቅጣጫ ተደርጎ እየተተገበረ ነው አሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፡፡
ከንቲባ አዳነች በአይነቱ የመጀመሪያና እጅግ ዘመናዊ የሆነውን የሕጻናትና ወጣቶች ቴአትርና ሲኒማ ኮምፕሌክስ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት መርቀን ሥራ አስጀምረናል ብለዋል።
በዚህ ወቅትም የከተማ አስተዳደሩ በሚሰራቸው የልማት ሥራዎች ሁሉ ኪነ ጥበብን አበይት የትኩረት አቅጣጫው አድርጎ እየተገበረ እንደሚገኝ ከንቲባዋ ተናግረዋል፡፡
ነባሮቹን በእድሳት ዘመናዊና ደረጃቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ በማድረግ እንዲሁም አዳዲስና ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ የተገጠመላቸው የቴአትርና የሲኒማ ኮምፕሌክሶችን በመገንባት ለኪነ ጥበብ ዘርፉ እድገት አስተዋጽኦ አበርክተናል ነው ያሉት።
የቴአትርና ሲኒማ ኮምፕሌክሱ ባለ14 ወለል ህንጻ ሲሆን ÷ 2 ዘመናዊ ሲኒማ ቤቶችን፣ የቴአትር አዳራሽ ፣3 የተለያዩ አዳራሾችን ፣ ሆቴል እና ሬስቶራንት፣ ዘመናዊ ካፍቴሪያዎችና የፓርኪንግ አገልግሎት መያዙን አስረድተዋል፡፡
የጥበብ ሥራ በአዳራሽ ብቻ የተወሰነ አለመሆኑን ጠቁመው÷ ወደ ማሕበረሰቡ እንዲቀርብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
ለአብነትም በመዲናዋ በተተገበረው ሁለንተናዊ ለውጥ የተለያዩ የውጭ የኪነ ጥበብ ሥራዎች የሚከወኑባቸው ከ160 በላይ አንፊ ቴአትርና ፕላዛዎች ተገንብተው ለአገልግሎት መዋላቸውን ጠቅሰዋል፡፡
ለኪነ ጥበብ ዘርፉ በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ የውስጥ ቁጭትን በመፍጠር ትውልድን በመልካም ሥራ እናንጽ ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡