በኢትዮጵያ ከተሞች በፍጥነት እየተስፋፉ ባሉ መደበኛ ባልሆኑ ሰፈራዎች ውስጥ ያለው የኑሮ ሁኔታ እጅግ አስከፊ መሆኑን የፖሊሲ ጥናት ተቋም (PSI) ባደረገው አዲስ ጥናት ይፋ አደረገ። ጥናቱ እንዳመለከተው፣ አብዛኞቹ ነዋሪዎች የራሳቸው ቤት ባለቤቶች ቢሆኑም፣ ለመሠረታዊ አገልግሎቶች ተደራሽነታቸው እጅግ ዝቅተኛ ነው።
የፖሊሲ ጥናት ተቋም ከ2018 ጀምሮ ሲያደርግ የነበረውን “በኢትዮጵያ ከተሞች ውስጥ የመደበኛ ያልሆኑ ሰፈራዎች መስፋፋት፡ ተግዳሮቶችና የፖሊሲ አማራጮች” በሚል ርዕስ የተካሄደውን ጥናት የመጀመሪያ ግኝት ላይ ዉይይት አካሄዷል።
በጥናቱ ከተካተቱት 1,067 ቤተሰቦች መካከል፣ 96.8% የሚሆኑት የራሳቸው ቤት ባለቤቶች እንደሆኑ ተመዝግቧል። ሆኖም፣ ለመሠረታዊ አገልግሎቶች ያለው ተደራሽነት እጅግ አሳሳቢ ነው። ንጹህና አስተማማኝ ውሃ የሚያገኙት 36.7% የሚሆኑት ብቻ ሲሆኑ፣ ፍላሽ መጸዳጃ ቤት ያላቸው ደግሞ 7% ብቻ ናቸው።
ሪፖርቱ አክሎም፣ 71.7% የሚሆኑት ሰፈራዎች የጎርፍ ማስወገጃ ሥርዓት ባለመኖሩ ለጎርፍ ተጋላጭ መሆናቸውን አጉልቷል።
የጥናቱ መሪ ተመራማሪ ዶ/ር ውባለም ስራው እንደገለጹት፣ የኢትዮጵያ የከተማ መስፋፋት መጠን 5.4% ሲሆን፣ ይህም ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ አገሮች አማካይ 4.1% በእጅጉ ይበልጣል።
ይህ ፈጣን ዕድገት በአብዛኛው የሚከሰተው ሕጋዊ የመሬት ይዞታ ወይም የማዘጋጃ ቤት ፈቃድ ሳይኖራቸው በሚገነቡ መደበኛ ባልሆኑ ሰፈራዎች መስፋፋት መሆኑን ተመላክቷል።
